ነገረ መላእክት

«መላእክት» የሚለው ቃል «ለአከ…ላከ» ከሚለው የግእዝ ሥርወ ግሥ የተገኘ ቃል ነው፤ ትርጕሙም እግዚአብሔርን ያለማቋረጥ የሚያመሰግንኑ ኀያላንና ረቂቃን መልእክተኞች ማለት ሲሆን «ነገር» የሚለው የግእዝ ቃልም፡- ሐሳብንና ምሥጢርን በጽሕፈት በአንደበት መግለጥ፣ በንባብ ማስጌጥ፣መልክ እያወጡ፣ ምሳሌ እየሰጡ ማብራራት ማለት ነው፡፡ /ኢሳ.6፥2፣ መጽ ሰዋ.ወግስ/

«ነገረ መላእክት» የሚሉት ሁለቱ ጥምር ቃላት ደግሞ የቅዱሳን መላእክቱን ተፈጥሮ፣ ክብር፣ ሀልዎት፣ አገልግሎት፣ ሥልጣን፣ ኀይልና ዕውቀት በስፋት የሚያጠናው ትምህርተ ሃይማኖት የሚብራራባቸው የተዋቡ ቃላተ ጽድቅ ናቸው፡፡

በመሆኑም በእግዚብሔር ፊት የተመረጡትን፣ የራሳቸውን አለቅነት በመጠበቅ የሚኖሩትን ቅዱሳን መላእክት ትምህርተ ሐተታ በሚቀጥሉት ንዑሳን አርእስት፣ በቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት በቅደም ተከተል እናያለን፡፡ /1.ጢሞ.5፥21፣ ይሁ..6/

ተፈጥሮተ መላእክት፡-

የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክትን ሲፈጥር እንደ ሰው በነቢብ በገቢር ሳይሆን በአርምሞ ነው፡፡ የተፈጠሩበትም ዓላማ እግዚአብሔርን ለማመስገን፣ የሰውን ልመና፣ ጸሎት፣ ንስሐ ወደ እግዚብሔር፣ የእግዚአብሔርን ምሕረትና ይቅርታ ወደ ሰው ለማድረስ ነው፡፡ /መዝ.90፥11፤103፥4/

መላእክትን በነገድ 100 አድርጎ ለአንድ ውዳሴ እና ቅዳሴ እና ቅዳሴ፣ለአንድ ኅብረትና ለአንድ ሃይማኖት፣ አንድ ጥበብ ባለበት ኅብረት ይኖሩ ዘንድ ፈጥሯቸው የነበረ ቢሆንም አንዱ ነገድ በራሱ ምርጫ ዓመፅን ሠርቶ፣ ከሉዓላዊ ክብር፣ ከመላእክት ማኅበር ተለይቶ እስከ ተላቁ ፍርድ ድረስ ከጨለማ በታች በእሥራት ለዘላለማዊ ውርደት ተዳርጓል፡፡ /2.ጴጥ.2፥2፣ራእ 12፥7-10/

በዕለተ እሑድ ሲፈተኑ «ንቁም በበህላዌነ እስከንረክቦ ለአምላክነ…አምላካችንን እስክናገኘው ድረስ በያለንበት ሆነን እንጽና» በሚለው አዋጅ በጽናት የለፉት 99ኙ ነገደ መላእክት ግን በማይናወጥ ኅሊና ለተፈጠሩለት ዓላማ በመታመን በአንድነት ጸንተዋል፡፡/አክሲማሮስ ዘእሑድ/

ተፈጥሯቸውም «ግብር እምግብር…ከተፈጠረ የተፈጠረ» ሳይሆን ያለምንም የፍጥረት ግኝት እምኀበ ወኢምንት ግብር /ካለመኖር ወደ መኖር/በርቀት የተፈጸመ መሆኑ ግልጥ ነው፡፡ /ሮሜ4፥17/

ከተልእካ ፍጥነተቸው፣ ከማይደክመው ኀይላቸው አንጻር በቅዱስ መጽሐፍ «ዘይሬስዮሙ ለመላእክቲሁ መንፈስ ወለእለ ይትለአክዎ ነደ እሳት…መላእክቱን መንፈስ፣ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል የሚያደርጋቸው» ተብሎ ይጻፍ እንጂ ቅዱሳን መላእክት ከባሕርያ ነፋስና ከባሕርያ እሳት አልተፈጠሩም፡፡ /መዝ104፥4/

ከነፋስና ከእሳትም እንዳልተፈጠሩ “እመሰ ተፈጥሩ እምነፋስ ወነድ እሞቱ ወእማሰኑ ከማነ… ከእሳትና ከነፋስ ተፈጥረውስ ቢሆን እንደእኛ በሞቱ በጠፉም ነበር”ተብሎ ተጽፏል፡፡ /መጽ፣ አክሲማሮስ/

ከተፈጠረ የተፈጠረ ሁሉ ይራባል፣ ይጠማል፣ ያረጃል፣ ይታመማል ይሞታል፡፡ መልእክት ግን በተፍጥሮአቸው የማያረጁና የማይመቱ ሕያዋን ስለሆኑ አይራቡም፣ አይጠሙም፣ አይታመሙም፣ ለዘመናቸውም ፍጻሜ አይነገርለተም፡፡

ኢመዋትያን መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ወአልባሙ መፍቅደ መብልዕ ሥጋዊ እስመ ኢካኑ ሥጋውያን … ረቂቃን መናፍስት እንጂ ግብር እምግብር የተፈጠሩ ግዙፋን አይደሉምና ሥጋዊ መብልንና መጠጥን መሻት በባሕርያቸው የለባቸውም፡፡ /ሃይ.አበ.36፥36፣ዜና ስክንድስ/

«ወሲሳዮሙኒ ለመላእክት ቅዳሴ ወስብሐት ወስቴሆሙኒ ፍቅረ መለካት… የመላእክት ምግባቸው ፈጣሪያቸውን ማመስገን፣ መጠጣቸውም የአምላካቸው ፍቅር ነው» ተብሎ መጻፉ የታመነና መጽሐፋዊ ምስክርነት ያለው እውነታ ነው፡፡ /መጽሐፈ አክሲማሮስ/

ሀልዎተ መላእክት፡-

በባሕርያቸው ኢ-መዋትያን ሆነው የተፈጠሩት፣ ለዘላለም አኰቴት /ምስጋና/ ጸንተው የሚኖሩት ቅዱሳን መላእክት የማይዳሰሱ ረቂቃን ቢሆኑም የማይለወጥ አካላዊ ህልውና አላለቸው፡፡ ለመንፈስ ሥጋና አጥንት ባይኖረውም ሀልዎተ መላእክት በረደኤተ ጻድቃን፣ በቅዱሳት መጻሕእት የተረጋገጠ ረቂቅ አካላዊ ህልውና ነው፡፡/ሉቃ 4፥39/

ዮሐንስ ዘደማስቆ የተባለው አባት ይኽን ሲያብራራ፡- «መላእክት ረቂቃን ናቸው የምንላቸው ከእኛ አንጻር ነው እንሀዳ ከማንም ጋር ከማይነጻጸተው ከእግዚብሔር አንጻር ሲታዩ ግን ግዙፋን ናቸው»ብሏል፡፡

ከፈጣሪያቸው አንጻር ግዙፋን ናቸው ቢባልም የወንድሃ የሰት ምልክት፣ አጥንት፣ ሥጋና ጅማት የሌላቸው ረቂቃን፣ የማያንቀላፉ ትጉሃን፣ የማይደክሙ ጽኑዓን ፍጥረታት ናቸው፡፡

«እነዚህ የእግዚአብሔር ሠራዊት ናቸው» የተባሉበት፣ እነደ ፀሐይ ደምቀው ከሰማይ ሲወርዱ የተዩበት ህልውሃቸውን የሚገልጠው፣ ግሩምና ድንቅ የሆነው አሰተርእዮ /መገለጥም/ በታላቁ መጸሐፍ ተመዝግባ ይገኛል፡፡ /ዘፍ32፥1-2፤ ዳን10፥6፤/

በመሆኑም በኀይል ብርቱዎችና በህላዌ ኢ-መዋትያን የሆኑት የብርሃናውየን መላእክቱ ህልውና በእውነተኛ ተፍጥሮ የተገኘ ክብርን የተሞላ እውነታ እንጂ የምናባችን ውጤት አይደለም፡፡

አለቅነተቸውንና ቦታቸውን የጠበቁት የቀዱሳን መላእክት ህልውና በዚህ መልኩ የሚገለጥ ቢሆንም በአንድ ጊዜ በሁሉም ቦታ የሚገኙ ምሉዓን አይደሉም፡፡

በአንድ ጊዜ ሁሉም ባታ ላይ እነደማይገኙም “እሙንቱሰ ሶበ ይትፌነው ለመልእክት ይትኀጥኡ እመካኖሙ…እነርሱስ መልእክት ለማድረስ በተላኩ ጊዜ ከቦታቸው ይታጣሉ”በማል ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ በድርሳኑ ገልጣታል፡፡/ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ/

ነገር ግን መላእክት በጊዜ በቦታ የሚወሰኑ፣ በመጠንና በልክ የተፈጠሩ ፍጡራን ቢሆኑም በሑሰት /በአሉበት ቦታ/ ሆነው በሌላው ቦታ ያለውን ሁኔታ የማየት፣የቦታ ርቀት ሳይጎርዳቸው የመረዳት ጸጋ የተሰጣቸው ግሩማን ፍጥረታት ናቸው፡፡/መጽ.መነኰሳት/

በመላእክት ህልውና ማመን ከፋርሶችና ከባቢሎናውያን ተወርሶ ወደ አይሁድ እምነት የገባ «የብዙ አማልክት ተረፍ ነው» በሚል አሰተሳሰብ በትንሣኤ፣ በመልአክና በመንፈስ መኖር እንደማያምኑት ረሲዓን /ዝንጉዎች/ ዛሬም በዚህ ዘመን የመላእክትን የምልጃ አገልገሎትና ህልውሃ የማይቀበሉ ስሑታን አሉ፡፡ /ሐመረ ክርስትና በመዋገደ ፍልስፍና/

ነገር ግን በምርጦቹ ቃል ኪዳን የምተምነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከቅዱሳት መጻሕፍት የተመነ ምስክርነት የተነሣ የቀዱሳን መላእክትን ህልውሃ አምና ታስተምራለች፡፡ /መዝ 86፥/

ለመታሰቢያም በስማቸው ሕንጻ ቤተክርስቲያን አንጻ፣ ታቦተ ሕግ ቀርጻ፣ መጻሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጋ ክብራቸውን፣ አገልግሎታቸውን፣ቀል ኪዳናቸውን እና ተራዳኢነታቸውን የሚያስተምረ ድርሳናቸውን ጽፋ በዓላቸውን ተከብራለች፡፡

የመላእክት ምልጃና ምስጋና፡-

ትጉሃን የማያንቀላፉት፣ ቅዱሳን መላእክት መልኩ በረድ በሚመሰለው መነበረ ስብሐት ያለ ድካም እንበለ ዕረፍት፣ አርምሞ ዕርዐት በሌለበት ፈጣሪያቸውን የሚያገለግሉ፣ ስለእኛ የሚማልዱ ኃያላን ፍጥረታት ናቸው፡፡ /ዕብ.1፥14/

ለአገልግሎትም ሲላኩ ሶበሰ ይወርዱ መላእክት እምሰማይ ዲበ ምድር አልቦሙ ድምፅ በኢይሰማዕ ድምፀ ክነፊሆሙ… መላእክት ከሰማይ ወደ ምድር በማወርዱበት ጊዜ ድምፅ የላቸውም፣ የክንፋቸው ድምፅም አይሰማም፡፡ ይቀልል ሩጸቶሙ እምነፋሳት…ሩጫቸውም ከነፋሳት ይልቅ የፈጠነ ነው፡፡/ራእይ 18፥1፣ ቅዱስ ያሬድ/

የዓለመ መንፈስ አካል የላቸው ብርሃናውያን መላእክት ወደ ላይ እስከ ጽርሐ ዓርያም ወደታች እስከ በርባሮስ ከመ ቅጽበተ ዓይን /እነደ ዓይን ጥቅሻ/ ደርሰው፣ መልእክታቸውን ፈጽመው ወደ ቦታቸው ይመለሳሉ፡፡ /ቅዱስ ኤጲፋንዮስ/

ለአገልግሎት ሲንቀሳቀሱም ከአካላቸው ረቂቅነት የተነሣ መገፋፋት እንደሌለባቸው ወየሐውር መልአክ በመልአክ.. መልአክ በመልአክ የልፋል፡፡/አክሲማሮስ/

በምልጃቸው የምናምነውን ሁሉ የሚጠብቁን፣ በኃጢአት ስንወድቅ «ለዛሬ ተዋት» እያሉ ስለእኛ መዳነ የሚማልዱልን፣ በእኛ ንስሐ መግባት በሰማያት ምስጋና የሚያቀርቡና ደስ የሚሰኙ ርኅሩኃን ፍጥረታት ናቸው፡፡ /ሉቃ.13፥7-9፣15/

በመሆኑም የመላእክት አገልግሎት፣አማላጅነት፣ተራዳኢነትና ሀልዎት ከ273 ጊዜ በላይ በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሰ ጥንታዊሃ ሐዋርያዊ መሠረት የለው ርቱዕ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ነው፡፡

ከምልጃ አገልገሎተቸውም ጋር ምስጋናቸው አርምሞ ጽርዐት የሌለበት ሲሆን “ዘወትር በዙፋኑ ዙሪያ ሆነው ያመሰግኑታል የማያርፉ መላእክትን ሁሉ በፊቱ ቆመው ሲየመሰግኑ ዓይኖቼ አዩ” ብሎ ረኣዬ ኅቡኣት /የተሰወረውን የሚያየው /ሄኖክ በዚህ መልኩ ገልጣታል፡፡/ራእ 4፥4-11/

ቅዱሳን መላእክት ፈጣሪያቸውን ሲያመስግኑ፣ሰውንና እግዚአብሔርን ሲያገለግሉ ተልእኳቸውን ዐውቀው የሚወጡ የሚወርዱ ስለሆነ «አልባቱ መልአክ ለመልአክ∙∙∙ለመልአክ» ደክሞሃል ብሎ የማየጸናው፣ውጣ ውረድ ብሎ የሚያዘው መልአክ የለውም፡፡/ድር∙ቄር∙61፥1/

የአገልግሎታቸው ኅብረ መልክም ልዩ ልዩ ነው፡፡ በየማዕረጋቸው፣ በየሠራዊተቸው፣ በየሥርዓታቸውና በየስማቸው የሚጋርዱ፣ የሚከቡ፣ የማያጠኑ፣ የሚዘምሩ፣ በልብ የሚየመሰግኑ፣ በቃል የሚያመሰግኑ ስፍር ቁጥር የሌላቸው በመንበሩ ዙሪያ የሚሰለፉ የቅዳሴ ማኅበርተኞች ናቸው፡፡ /ቅዱስ አትናቴዎስ/

ቁጥራቸው እልፍ አእላፍ የብዙ የሆነው ሰባሕያን መላእክቱ ከላይ በራእየ ሄኖክ እንደተገለጠው ቅዱስ ዮሐንስም «ወሰማዕኩ ቃለ መላእክት ብዙኃን በዓውዱ ለውእቱ መንበር∙∙∙ በዚያ መንበር ዙሪያ የመላእክትን ቃል ሰማሁ፤ የአራቱ እንስሳንና የ24ቱን ሊቃናት ድምፅ ሰማሁ፣ ቁጥራቸውም እልፍ አእላፍ የብዙ ብዙ ነው፤ በተላቅ ቃል ባዕል፣ ጠቢብ፣ ጽኑዕ፣ ንጉሥ፣ ክቡር፣ ስቡሕ፣ ቡሩክ መባል፣ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይገባዋል አሜን እያሉ ሲናገሩ ሰማሁ» በማለት አብራርቶታል፡፡/ራእ∙5፥12/

ከማያቋርጠሙ ምስጋና ጋር በየማነ ምስዋዕ /በመሠዊያው ቀኝ/ቆመው «እለ ይስእሉ ምሕረተ ለውሉደ ሰብእ∙∙ለሰው ልጆች ሁሉ ምሕረትን የሚለምኑ፣ ለነፍሳት መዳን የሚቆሙ» ለይቅርታ የተዘጋጁ፣ ለምሕረት የሚላኩ ናቸው፡፡ /ሉቃ 1፥11-2ዐ/

በአምላካቸው ፊት በባለሟልነት የሚቆሙት፣ጸሎተ ቅዱሳንን የሚያሳርጉት ቅዱሳን መላእክት ምልጃ ለሰው ብቻ ሳይሆን «ለእንስሳ ሣዕረ ለሰብእ ተግባረ∙∙∙ለእስሳ ሣርን፣ለሰው በጎ ተግባርን» ይለምናሉ የሰውን በጎ ሥራ ሁሉ ያሳርጋሉ፡፡/ቅዱስ ጋሬድ/

ለዘለዓለም ያለ ድካም የለ ዕረፍት ቅዱስ እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ይኖራሉ፡፡ ምስጋናቸው እና ጸሎተቸውም ሁል ጊዜም በእግዚአብሔር ፊት የሚቀርብ ነው፡፡/ኢሳ∙6፥1-5፣ራእ 4፥8/

ክብረ መላእክት፡-

በተለየ ክብር የማማለድና የመተደግ ሥልጣን ያላቸው በባለሟልነት በእግዚአብሔር ፊት የማቆሙት መላእክት ንዑዳን ክቡራን፣ ረቂቃንና ምሉዓነ ኀይል ናቸው፡፡ /ሉቃ∙1፥∙∙1∙ጢሞ 5፥21/

ሰዎች ድኅነትን በሚየገኙ ጊዜ ደስ የሚሰኙት ብርቱዎቹና ኀያላኑ የከበሩት መላእክት የሰው ልጅ በክብሩ በሚመጣበት ጊዜ ከእርሱ ጋር በክብሩ ዙዳን ይቀመጣሉ፡፡/መዝ∙1ዐ3፥2ዐ፣ማቴ∙25፥31/

ፍጥረተ ሰብእ በከተማ ኀጢአት እንዳይጠፋ በማያደርጉት ትድግና፣በትሕትናቸው በአገኙት ልዕልና ለዘላለም የከበሩ ብርሃናውያን ናቸው፡፡/ዘፍ∙19፥15፣ቅዱስ ያሬድ/

ቅዱሳን መላእክት ድል ነሺዎቹና ለራሳቸው ክብር የማይኖሩት የከበሩት ፍጥረታታ የሚሰግዱላቸውና የከበሩ መሆናቸውበቅዱሳት መጻሕእት የተመዘገበ፣ በእውነት ያለ ሐሰት የተረጋገጠ ነው፡፡ /ራእ 19፥1ዐ/

«የሰው ልጅ መላእክቱን ይልካል ከመንግሥቱም እንቅፋትን ዓመፃን የሚያደርጉትን ሁሉ ይለቅማሉ፣ ከዐራቱ ነፋሳት ለእርሱ የተመረጡትን በክብር ይሰበስባሉ»ተብሎ እራደተጻፈው በክብራቸው የተመረጡትን ለክብር ይሰበስባሉ፣ ዓመፀኛውንም ለይተው ለዘላለም ፍርድ ያቀርባሉ፡፡/ማቴ∙13፥41፣24-31/

ክቡራን መላእክቱ ሰውን ከሚያስጨንቀው፣ ከክብር ከሚያሳንሰው ነገር እና ዝንጋዔ የራቁ፣ ባለአእምሮ የኾኑ፣ ዕውቀት የላቸው፣ ይዋሄንና ትዕግሥትን ገንዘብ ያደረጉ፣ ለዘለዓለም በማይነጥፍና በማያቋርጥ ዘወትር እንደዥረት ውኃ በሚወርድ ምስጋና ይኖራሉ፡፡ በመሆኑም የቀዱሳን መላእክት ክብራቸው ታላቅ ስለሆነ ኀጢአጽ ስንሠራ ይቅር የማይሉ ናቸውና እንዳናስመርራቸው በፊታቸው ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ /ዘጸ23፥2ዐ/

የመላእክት ኅይልና ሥልጣን፡-

የቅዱሳን መላእክት ኀይልና ሥልጣን ምንጩ ገባሬ መላእክት እግዚአብሔር ነው፡፡/2∙ጴጥ∙2፥11/ የእግዚአብሔር ስም በእነርሱ የሆነላቸው መላእክት የሥልጣናቸውና የኀይላቸው መጠነ ክሂል «በፊቱ ተጠንቀቁ ፣ቃሉንም አድምጡ ኀጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልም» በሚል የተገለጠ፣ማንም ሊሽረው የማይችለው ሥልጣን መሆኑ የታወቀ ነው፡፡/ዘጸ 23፥2ዐ/

የመላእክቱ ኀይልና ሥልጣን በግብር ሲታይ ለተቀበሏቸው የምሥራች፣ ምሕረትን፣ ከእስራት መፈታትን የሚያድል፣ ክብርንና ሞገስን የሚያሰጥ ሲሆን በጊዜው የሚፈጸመውን ቃል /ነገር/ ለማይቀበሉት ደግሞ ዲዳ እስከመሆን የሚያደርስ፣ ለእግዚአብሔርና ለመላእክቱ ክብር ባልሰጡ መጠን በእደ መላእክት ተመትቶ፣ በትል ተበልቶ መሞትን ያስከትላል፡፡ /ሉቃ 1፥19፤የሐ∙ሥ 12፥23/

የመላእክቱን ኀይልና ሥልጣን ማከበር የሚያሰደንቀውን እንዲህ ያለ ሥልጣን የሰጠውን እግዚአብሔርን ማከበር ነው፡፡ /ማቶ 9፥8/ ይህም ሥልጣን ለመላእክት የተሰጠው ፍጥረተ ሰብእን ለመጠበቅና ለማገልገል ነው፡፡ክቡር ሆኖ የተፈጠረው የሰው ልጅ ሲፈጠር ጠባቂን አይሻም ነበር፡፡

ሰው በኃጢአት ከወደቀ በኋላ ግን እግዚብሔር መላእክትን ጠባቂ አደረገለት፡፡ ምክንያቱም ዲያብሎስ ሰውን ለማጠፋት ሁል ጊዜ ምክንያቶችን ስለሚፈልግ ነው፡፡/ቅዱስ ጎርጎርዮስ/

በመሆኑም መጎደላችን ከሥጋና ከደም ጋር ሳይሆን ከመንፈሳዊ ክፋት ኃይላትና ከጨለማ ገዢዎች ጋር ነውና ቅዱሳን መላእክት በሰይጣን እንዳንታለል የሚጠብቁን፣ ይልቁንም የእግዚአብሔርን ፍቅርና እንክብካቤ በምናይበት ሁኔታ ያለመታወክ በጸጥታ ኖረን መዳንን እንወረስ ዘንድ በረድኤታቸው የሚያግዙንና የሚያገለግሉ መናፍስት ናቸው፡፡/2ቆሮ 2፥11፤ዕብ 1፥11/

ነገር ግን ሰይጣን ራሱን የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና በመላእክትና በአጋንንት መካከል የለውን ልዩነት ማወቀ በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡/2ቆሮ 11፥14-5/

ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራን እግዚአብሔር በዘመን ፍጻሜ ወደ እርሱ እስኪጠቀልለነ ድረስ በማያሰናክለው ዓለም ስንኖር የሚረዱንን ቅዱሳን መላእክት በተመለከተ የተሟላ መንፈሳዊ ዕውቀት ያስፈልገናል፡፡

ለማወቅም «ወአንተሰ ለእመ ትፈቀድ ታእምር ኀድግ ኅሊና ዘበምድር ∙∙∙አንተ ግን ማወቅ ከፈልግህ ምድራዊ አስተሳሰብን ተው» ተብሎ ተጽፏል፡፡/1ጴጥ 5፥1ዐ፤ ኤፌ 6፥12፣ ቅዱስ ያሬድ/

በአጠቃላይ የምድራዊ አሰተሳሰብን በመተው የምንረዳው የመላእክት ተልእኮ በጥቅሉ ሲገለጥ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ሆነው የሰውን ጸሎት፣ ምጽዋትና ምሥዋዕት ማሳረግ፣ በመከራና በችግር ጊዜ ለተራዳኢነት ወደ ሰዎች መላክ፣ ሰዎች ዘዚህ ዓለም በሞት ወደ እግዚአብሔር ሲሄዱ ነፍሶቻቸውን ወደ እርሱ ማቀረብና በፍጻሜ ዘመንም ኀጥዓንን ከጻድቃን ለመለየት የሚላኩ ናቸው፡፡ /ማቴ∙24፥31፤ሐዋ2፥7፤ሮሜ∙9፥22/

ወስብሐት ለእግዚአብሔር