መድኃኔዓለም

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መድኃኔዓለም”ብላ ስትጠራው ” የዓለም ኹሉ መድኃኒት አንተ ነኽ” እያለች ነው።
ይኽም ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መላውን ዓለም ከዘላለም ሞት፣ ከሲኦል ባርነትና ከሰይጣን አገዛዝ ነፃ ያወጣበትን ታላቅ የማዳን ሥራ የሚገልጽ ስም በመኾኑ ነው።
​ለዚህም ስያሜ መነሻ የሆናት ቅዱሱ መጽሐፍ ሲሆን ይኸውም ክብር ይግባውና እርሱ ገና ​በጽንሰቱ፤ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለቅዱስ ዮሴፍ “ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ” (ማቴ ፩፡፳፩) በማለት የመድኃኒትነት ስሙን ከነ ግብሩ አብስሯል።
በዚኽ ያላበቃው ቸርነቱ ​በልደቱም ቀጥሎ እርሱ በተወለደ ጊዜ መላእክት ለእረኞች “ለሕዝቡ ኹሉ የሚኾን ታላቅ ደስታ… መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋል” (ሉቃ ፪፡፲) በማለት የዓለም መድኃኒትነቱን መስክረዋል።
ኋላም በመዋዕለ ሥጋዌ ​ትምህርቱ፤ ሳምራዊቷ ሴት ያደረገላትን ነገር ኹሉ ለሴቶቹ ከመሰከረችላቸው በኋላ “አኹን የምናምን ስለ ቃልሽ አይደለም፥ እኛ ራሳችን ሰምተነዋልና፤ እርሱም በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደ ኾነ እናውቃለን ይሉአት ነበር።”
(ዮሐ. ፬፥፵፪)
መድኃኔዓለም አባታችን በቤታችን የጎደለውን በምሕረቱ ይሙላልን።
የጎበጠውን ኑሯችንን ያቅናልን።
በእልፍኛችን ተሸሸግን ያነባነውን እንባችንን ያብስልን።
አሜን