
በዘመናት ጉዞ በማዕበል እየተመታች፣ ፈጽሞ ያልሰመጠች መርከብ ብትኖር እርሷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ናት። የዚኽ ኹሉ መሠረት ደግሞ ‟ አናቅጸ ሲኦል ኢይኄይልዋ፤ የገሃነም ደጆች አይችሏትም”(ማቴ.፲፮፥፲፱) በማለት ለቤተክርስቲያን በተነገረላት የአምላክ ቃል ኪዳን ነው።
“You will burn and you will burn out; you will be healed and come back again.” እንዳለ ደራሲው ‘ርግጥም ቤተክርስቲያን ሲያቆስሏት፦ ድና ሌላውን እየፈወሰች፣ ሲቀጥፏት፦ አብባ እልፍ እያፈራች፣ ሲረግሟት፦ መርቃ እየባረከች፤ ሲያነዷት ደምቃ እያበራች፤ከየዘመናቱ ርዕዮተ ዓለም ታግላ፥ ከኑፋቄ ተፋልጣ፤ለሐቅ ተጋድላ ከታሪክ ተጣምራ፤እዚኽ ደርሳለች።
የመድረሷ ምስጢርም ከአምላካዊ የኪዳኑ ጠብቆት ጋር፤ የቅዱሳን አባቶቻችን ነፍሳቸውን እንደ ኢምንት ነገር እንኳ ሳይቆጥሩ ለቤተክርስቲያን ባደረጉት ታላቅ ተጋድሎ ነው።
የእግዚአብሔርን ቃልየተናገሩአችኹን ዋኖቻችኹን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው።”(ዕብ. ፲፫፥፯)ይላልና ቃለ እግዚአብሔር፤ በዚኽ አጠር መጠን ባለ ገጸ ንባብ ፤ በዜማ በኩል ከያሬድ በኋላ የተነሣ ❝ ዳግማዊ ያሬድ ❞ የተባለ እና በዘመኑ የነበሩ መናፍቃንን በመከራከርና በመርታቱ ❝ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ ❞ (ገድለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና ገድለ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል፤ ፳፻፬ ዓ.ም ገጽ 12) ።
በዚህ የሚጠራውና የተሰጠው ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሊቅና ጻድቅ አባት፣ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫን ሕይወት እና ሥራዎች እንመለከታለን።
ልደቱ
በ፲፭ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ የጥበብ ሰማይ ላይ እንደ ንጋት ኮከብ ደምቆ የበራ፣ የእውቀቱ ጥልቀት እንደ ውቅያኖስ የማይመረመር! የመንፈሱ ግርማ እንደ ደብረ ታቦር ብርሃን የሚያንጸባርቅ አንድ ታላቅ ሊቅ ተነሥቶ ነበር እርሱም አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ነው። (በመ/ር በኃይሉ በቀለ:2018 ዓ.ም ገጽ: 162)።
ይኽ ታላቅ አባት የተነሣበት ዘመን በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ታሪክ ወርቃማው ዘመን ተብሎ ከሚጠራበት ጊዜ አንዱ ነው። (ዲ/ን ሰሎሞን ዮሐንስ: 2001 ዓ.ም፡ ገጽ 145 -185)
ምክንያቱም በጨለማው ዘመን ወይም (ከ፯ኛው-፲፩ኛው መ/ክ/ዘ) ተገትቶ የነበረው የግዕዝ ሥነ ጽሑፍ ያንሰራራበት፤ የክርስትና እምነት በአዲስ መልኩየተጠናከረበት፤ከግብፅ ቤተክርስቲያን ጋር የነበረን ግንኙነት እንደገና እየታደሰ የኼደበት፤ የብህትውና እና የምንኩስና ሕይወትም እያደገ የመጣበት፤ በጣና ሐይቅ ዙሪያ ታላላቅ ገዳማት የተተከሉት ..ወዘተ ስለነበር።(ዝኒ ከማሁ፡ገጽ 145 -146)
አባ ጊዮርጊስ ገድል ስለተጻፈላቸው ማን እንደኾኑ ለማወቅ ይቻላል፤(ጌታቸው ኃይሌ 2012፡ገጽ 233).
ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ከሕዝበ ጽዮን እና ከእምነ ጽዮን በ1357 ዓ.ም (ግድም ይላሉ ጌታቸው ኃይሌ) ተወለዱ። የአባ ጊዮርጊስ ወላጆች ልጅ ስላልነበራቸው ዘወትር እግዚአብሔርን በጸሎት ሲጠይቁ ኖረው የተሰጣቸው የጸሎት ፍሬ፡ የተማጽኖ ውጤት፣ የስለት ልጅ ነው።(አሻግሬ አምጤ፣ 2017፣ ገጽ 94).
አባቱ በሸ/ሰግላ ውስጥ በነበረች ደብረ ማህው በተባለች አምላክን በወለደች በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በተሠራች ቤተክርስቲያን ውስጥ በነበረ የመላእክት አለቃ የቅዱስ ዑራኤል ሥዕል ፊት ተንበርክኮ በማልቀስ ያገኘው የስለት ልጅ መኾኑን…ድርሳነ ዑራኤል ዘሰኔ ያስነብበናል ።(ዝኒ ከማሁ: ገጽ 94)
ሸግላ/ሰግላ ማለት በአሁኑ ደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በቦረና አውራጃ በከለላ ወረዳ በወለቃና በበቶ ወንዝ መካከል በምትገኝ ልዩ ስሟ ሸግላ/ሰግላ/ ተብላ የምትጠራ ደብረ ማኅው የተሰኘች አካባቢ ነው፡፡(ገድለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና ገድለ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል፤ ፳፻፬ ዓ.ም ገጽ, 9)
እናቱ እመነ ጽዮን ልጇ እንደ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ የእውነት ምስክር እንዲኾንላት በመመኘት ጊዮርጊስ ብላ ስም አወጣችለት። ስሙ ብቻ ሳይኾን ግብሩም ጊዮርጊስን ይመስል ዘንድ ፈሪኻ እግዚአብሔርን እያስተማረች፡ በጥበብ እና በዕውቀት አሳደገች።
❝ ጉዞ ወደ ትምህርት ዓለም ❞
አባቱ ሕዝበ ጽዮን ልጁን መጻሕፍትን በማንበብና በመተርጎም ረገድ በጣም ጠቢባንና የተካኑ ወደተባሉ ካህናት መምህራን ወዳሉበትበጊዜው በኢትዮጵያ ታላቅ የትምህርት ማእከል በነበረችው ሐይቅ ደብረ ነጐድጓድ ገዳም ወደምትገኘው ትምህርት ቤት ይዘዋቸው በመሔድ ከታላቁ ሊቅ ዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ጋር እንዲማሩላቸው አድርሰዋቸው መጡ፡፡
ለትምህርት ሐይቅ የገባው በዐፄ ዳዊት /1365-1395 ዓ.ም/ ዘመነ መንግሥት አባ ሠረቀ ብርሃን ገዳሙን በሚያስተዳድርበት ዘመን ነበር። አባ ሠረቀ ብርሃን የተማረ ብቻ ሳይኾን ለቀናች ሃይማኖት ተቆርቋሪና ድጋፍ ነበር። በእርሱ ዘመን እዚያ መማር መታደል ነበር። ጊዮርጊስ በትምህርት ብቻ ሳይኾን በቀናች ሃይማኖትም ለመቀረጽ መልካም አጋጣሚ ኾኖለታል።(ሥርግው ሐብለሥላሴ (ዶ/ር) : 2018:ገጽ, 772)
እንደ ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት ጥናት ጽሑፍ አባቱ ሕዝበ ጽዮን በቤተ መንግሥት ከነበሩ የንጉሥ ካህናት አንዱ ስለነበር፣ ወጣቱ ጊዮርጊስ የመጀመሪያዎቹን የልጅነት ጊዜያቱን ያሳለፈው በቤተመንግሥት መኾኑን ሲነግረን፤
(Taddesse Tamrat, 1972, p. 437)
ዲ/ን አሻግሬ አምጤ ደግሞ፤ አባቱ ነገሥታት በየኼዱበት አብራ እየኼደች በድንኳን ትኖር በነበረችው ሥዕል ቤት ያገለግሉ ከነበሩ ካህናተ አንዱ እንደነበር ይነግረናል።(አሻግሬ አምጤ፣ 2017፣ ገጽ 95).
❝ ትምህርት ዓለም ፈተና ❞
አባ ጊዮርጊስ ከ1374 – 1407 ዓመተ ምሕረት የኢትዮጵያ ንጉሥ በነበረው በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ለተጨማሪ ትምህርት ከዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ዘንድ ሐይቅ እስጢፋኖስ ከገቡ በኋላ፣ ብዙ መጻሕፍት ከነበሩበት እና ታላላቅ ሊቃውንት ተምረው ከወጡበት ትምህርት አልገባኽ ብሏቸው ለሰባት ዓመታት ተቀመጡ። (ዝኒ ከማሁ:ገጽ 98)
በወቅቱ አብረዋቸው ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች ተምረው እየተዋቸው፣ ከእርሳቸው በኋላ ትምህርት ቤት የገቡትም እያለፏቸው ይኼዱ ነበር። ትምህርት አልገባኽ ስላላቸው አብረው ይማሩ የነበሩት ተማሪዎች ብቻ ሳይኾን እኽል እየፈጩ፣ ውኃ እየቀዱ እና እንጨት እየለቀሙ ያገለግሏቸው የነበሩ የገዳሙ መነኰሳት ጭምር ይሳለቁባቸው ነበር።
በዚኹ ምክንያት በሐይቅ እስጢፋኖስ ወንበር ዘርግቶ ያስተምር የነበረው ዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ለአባቱ ” ልጅህ ትምህርት ስለማይገባው የቤተ መንግሥት ሥርዓት አስተምረው” በማለት ወደ ቤት ሲመልለሷቸው የጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ወላጅ አባት ሕዝበ ጽዮን ግን “ አንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር ስለሰጠሁት” እዚያው እየኖረ ገዳሙን ያገልግል በማለት መልሶ ወደ ገዳሙ ላከው።(ዝኒ ከማሁ:ገጽ 98)
❝ ታሪክ ሲቀየር ❞
ከየአቅጣጫው የደረሰባቸው መገፋት ጊዮርጊስ ዘጋሥጫን ወደ ገዳሙ ተመልስው ከሥዕለ ማርያም ሥር እየተደፉ መማጸን የዘወትር ተግባራቸው ኾነ፡፡እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም የቅዱሱን ከሥዕሏ ሥር እየተደፉ ማልቀስ በከንቱ አላስቀረችም።
ከዕለታት አንድ ቀን ከመልአኩ ከቅዱስ ዑራኤል ጋር ተገልጣ “ልጄ ጊዮርጊስ ኾይ አይዞኽ፣ ዕውቀት የተሰወረብኽ ትምህርት የማይገባኽ ኾነኽ ሳይኾን የእግዚአብሔር ድንቅ ተአምር በአንተ ይገለጥ ዘንድ ነው።” ብላ በተናገረች ከሰባት ቀን በኋላ፤
በግዕዙ እንደሚለው ❝ ወአመ ሰትየ ውእቱ ጽዋዐ አእምሮ እምእደ እግዝእትነ እመ ብርሃን ❞ /ከብርሃን እናት እመቤታችን እጅ የዕውቀት ጽዋን በጠጣ ጊዜ/
“…ወእምይእቲ ሰዓት ተከሥተ አዕይንተ ልቡ ወተመሰጠ ኅሊናሁ በአክናፈ መንፈስ ቅዱስ፡፡
ወበጽሐ ኀበ ኅሊናሁ ለአብ ወበህየ ረከበ ኢየሱስሃ እንዘ ይነብር በየማነ አቡሁ ወጰራቅሊጦስሃ ኅቡረ በህላዌሁ…” (ገድለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና ገድለ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል፤ ፳፻፬ ዓ.ም ገጽ 42)
ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ የልቡ ዓይን በራለት፡፡ ተከፈተለት ኅሊናወም በመንፈስ ቅዱስ ክንፎች ተመሰጠ፡፡ ወደ አብም ደረሰ፤ በዚያም ኢየሱስን በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ጰራቅሊጦስንም በአንድ አኗኗር አገኘው፡፡
ከዚያችም ቀን ጀምሮ አባታችን ጊዮርጊስ የመጻሕፍትን ንባባቸውንና ትርጓሜያቸውን አስተዋለ፡፡(ዝኒ ከማሁ፡ ገጽ 43)
እንደ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ጽሑፍ አባ ጊዮርጊስ የኋላ ኋላ ትምህርት የቀናላቸው ስለ ኹለት ነገር ነው።
አንደኛው ምክንያት ከላይ እንደጠቀስነው ከእመቤታችን ሲኾን ኹለተኛው ምክንያት ደግሞ “እስመ እንበለ መከራ
ኢይትወሀብ ጸጋ ወእንበለ ተፈትኖ ኢይከውን አፈድፍዶ” (ያለ መከራ ጸጋ አይሰጥም፤ ያለ መፈተን የተገኘውን ማብዛት አይቻልም) ይለዋል።(ጌታቸው ኃይሌ:2012፡ገጽ 233).
ክፍል ፫ ይቀጥላል…