የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ኅትመት አጀማመር ታሪካዊ ዳሰሳ፣
መግቢያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዶግማዋን፣ ቀኖናዋን፣ ትምህርቷን፣ ትውፊቷን፣ ታሪኳን እና መንፈሳዊና ልማታዊ አገልግሎቶችን ለተከታይ ምእመናኖቿ በኅትመት ሚዲያ ስታስተምር መቆየቷን ታሪክ ያስረዳል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ኅትመት ሚዲያ ታሪክ ከ፲፱፻፴/1930ዎቹ ጀምሮ የሚጠቀስ ሲኾን በዚህ ዓመታት ውስጥ በርካታ የኅትመት ውጤቶች እየታተሙ ለምእመናን ይሠራጩ ነበር፡፡
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምያ ለመጀመሪያ ጊዜ በትምህርተ ሃይማኖት ላይ ያተኮረ ‹‹ተክለ ሃይማኖት›› የተሠኘ ጋዜጣ ኅዳር ወር ፲፱፻፴፰/1938 ዓ.ም ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡
በመቀጠልም በ፲፱፻፵/1940 ዓ.ም ‹‹ዜና ፡ ቤተ ፡ ክርስቲያን ፡ ዘኢትዮጵያ›› ጋዜጣ መታተም ጀመረ ሲኾን ዜና፣ የክብረ በዓላት ታሪክ፣ ወቅታዊ ዘገባዎች፣ እና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሚያቀርብ ነበር፡፡ እነዚህ ጋዜጦች በየ፲፭/15 ቀኑ እየታተሙ ይሠራጩ የነበረ ሲኾን በሂደትም ወደ አንድ ጋዜጣነት ተጣምረው በየሳምንቱ እሑድ እንዲወጡ ተደርጎ ነበር፡፡
ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በቤተ ክርስቲያን ኅትመት ሚዲያዎች ዕድሜ ጠገብ እና በታሪክም ትልቅ ሥፍራ የሚይዝ ነው፡፡ ዜና ቤተ ክርስቲያን በረጅም ታሪኩ በርካታ ዓምዶችን በመክፈት የተለያዩ ርእሰ ጉዳዮችን በስፋት ሲያስተናግድ የቆየና የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሳን ኾኖ የዘለቀ አንጋፋ የሕትመት ሚዲያ ነው፡፡
ጋዜጣው በዋነኛነት የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥራ ሓላፊዎች የሚያከነወኗቸው ሥራዎችን ፣ ጉባኤዎችንና ስብሰባዎችን ፣ እንዲሁም በአህጉረ ስብከትም ኾነ በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚከናወኑ ልማታዊና መንፈሳዊ እንቅስቀሴዎችን በመዘገብ ለአንባብያን ሲያደርስ የቆየ መንፈሳዊ ጋዜጣ ነው ፡፡
ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በሀገራችን እንደ ዛሬው የሚዲያ አማራጭ በሌለበት በዚያ ዘመን የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም ተግባር እየዘገበ በማስነበብ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ክብር ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን በማስተዋወቅ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል ፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በማኅበራዊ አገልግሎት ተደረሽነቷ ፣ በተለይም በድርቁ ዘመን ለተጎዱ ወገኖች ታደርገው የነበረውን ሰብአዊ ድጋፍ በዜና ሽፋን ከትቦ ለመላው ዓለም በማሳወቅ ረገድ ፣ ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ያከናወነው ተግባር በወቅቱ ተወዳዳሪ አልባ ጋዜጣ እንዲኾን አስችሎታል ፡፡
ዓምዶች፣
ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በዋነኛነት የሚያተኩረው የዜና ሽፋን በመዘገብ ላይ ቢኾንም የጋዜጣው ወቅታዊ መልእክት ማስተላለፊያ በጥንቱ ርእሰ ነገር በኋላም ርእሰ አንቀጽ የተሰኘ ዓምድ ይዞ ዘልቋል፡፡
በተጨማሪም የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር የሚሻሻልበትን ፣ የገቢ ምንጭ የሚስፋፋበትን ፣ መሪዎቿ የሚመረጡበትንና በተሐድሶ ጎዳና የምትራመድበትን መንገድ በማብራራት እና በማስረዳት የሚቀርቡና የቤተ ክርስቲያንን ታሪክም ኾነ የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ትምህርት በጠቅላላውም መንፈሳዊውን ፍልስፍና ተተንትነውና ተመሥጥረው ለግንዛቤና ለምርምር የሚቀርቡ ጽሑፎች የሚሠፍርበት፡- ‹‹ተሐድሶ ፡ ዓምድ ፡ ለውይይት›› በኋላም ‹‹የተሐድሶ ፡ ዓምድ ፡ ለውይይትና ፡ ለትምህርት›› የተሰኘ ዓምድ እስከ ፲፱፻፹፩/1981 ዓ.ም ይዞ ዘልቋል፡፡
እንዲሁም በተለያዩ ጊዜያትም የተለያዩ ዓምዶችን በመክፈት ጽሑፎችን ያሰፍር የነበረ ሲኾን፡-
‹‹ከመንፈሳዊ ፡ ዓለም›› ፣
‹‹የሴቶች ፡ ዓምድ›› ፣
‹‹ምን ፡ ይላሉ ? የአስተያየት ፡ ዓምድ›› ፣
‹‹ኢትዮጵያ ፡ በዘመነ ፡ ኦሪት ፡ የታሪክ ፡ ዓምድ›› ፣
‹‹የሊቃውንት ፡ ዓምድ›› ፣
‹‹ወጣቶችና ፡ ቤተ ፡ ክርስቲያን ፡ የወጣቶች ፡ ዓምድ›› ፣
‹‹ኢትዮጵያ ፡ በዘመነ ፡ ሐዲስ ፡ የታሪክ ፡ ዓምድ››
‹‹ትዝብትና ፡ ምክክር ፡ ዓምድ›› ፣ የመሳሰሉትን ዓምዶች በመክፈት ትምህርትንና ታሪክን ለትውልድ ሲያስተላልፍ ቆይቷል፡፡
አዘጋጆች፣
ከጋዜጣው ምሥረታ ጀምሮ በርካታ በቤተ ክርስቲያንንም ኾነ በዘመናዊ ትምህርት አንቱ የተሠኙ አንጋፋ ሊቃውንት የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ፣ ምክትል አዘጋጅ እና የጽሑፍ አዘጋጅ ኾነው ተሳትፈውበታል፡፡
በምሳሌነት ለመጥቀስ ያክል፡-
በ፲፱፻፶/1950ዎቹ ዓ.ም አባ ተፈራ (ገብረ ሕይወት) መልሴ፣ ቀሲስ ክንፈ ገብርኤል አልታየ ናደው (ሊቀ ካህናት) ፣
በ፲፱፻፷/1960ዎቹ ደግሞ የጋዜጣው ዕድገት ጠባቂዎች በሚል ፩ኛ ቀሲስ ሰሎሞን ገብረ ሥላሴ ፣
፪ኛ አቶ ኢሳይያስ ዓለሜ፣
፫ኛ አለቃ ብርሃኑ መኰንን ፣
ዋና አዘጋጅ ፡- ቀሲስ ክንፈ ገብርኤል አልታየ (ሊቀ ካህናት) ቀጥሎም ፡-
፩ኛ ክቡር አቶ መኰንን ዘውዴ ፡- በም/ሚኒስቴር ማዕረግ የጠ/ቤተ ክህነት ም/ሥራ አስኪያጅ ፣
፪ኛ ዶክተር ዕጓለ ገብረ ዮሐንስ፣
፫ኛ አቶ ኢሳይያስ ዓለሜ ፡- የታሪክ፣ ድርሰትና ስብከት ክፍል ሹም ፣
ዋና አዘጋጅ ፡- ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ (መጋቤ ምስጢር) በመቀጠልም ፡-
፩ኛ ክቡር ንቡረ ዕድ ኤርምያስ ከበደ ፡- የጠ/ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ ፪ኛ ዶክተር ዕጓለ ገብረ ዮሐንስ ፡- በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካሪ ፣ ፫ኛ ቀሲስ ሰሎሞን ገብረ ሥላሴ ፡- የታሪክ፣ ድርሰትና ስብከት ክፍል ተ/ሹም ፣ ዋና አዘጋጅ ፡- ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ (መጋቤ ምስጢር) ኾነው የጋዜጣውን ሕትመት ያስቀጠሉ ሲኾን ዋና አዘጋጅ ኃይለ ልዑል ወልደ ገሪማ፣ ተ/ዋና አዘጋጅ ይቁም ግዛው ፣ እንዲኹም ም/አዘጋጅ መልአከ ምሕረት ዓምደ ብርሃን ገብረ ጻድቅ የመሳሰሉት ሊቃውንት በመሪነት ተሳትፈውበታል፡፡
በተለይም መጋቤ ምሥጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ ለረጅም ዓመታት የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ ኾነው በማገልገል የጋዜጣው ምልክት እስከ መኾን የደረሱ ናቸው፡፡
ሥያሜና አርማ፣
የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ኅትመት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የጋዜጣው ስም እና አርማ (ሎጎ) በየጊዜው እየቀያየር መጥቷል፡፡
በጥንቱ፡- ዜና ፡ ቤተ ፡ ክርስቲያን ፡ ዘኢትዮጵያ ፡ በሚል ሥያሜ አርማው (ሎጎው) የእጅ መስቀል የነበረው ሲኾን በሂደትም አርማው (ሎጎው) የቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ፣ ሠናይ ፡ እገሪሆሙ ፡ ለእለ ፡ ይዜንው ፡ ሠናየ ፡ ዜና ፡ ሮሜ ፡ ም፡ ፲ ቍ ፲፬ የሚል መሪ ቃል በክብ ቅርፅ ተጽፎበት ይታተም ጀመረ፡፡
በመጨረሻም፡- አርማው (ሎጎ) የቤተ ክርስቲያን ጉልላት መስቀል ኾኖ ‹‹ሠናይ ፡ እገሪሆሙ ፡ ለእለ ፡ ይዜንው ፡ ሠናየ ፡ ዜና››፡፡ መልካሙን የምሥራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው ፡፡ የሚል መሪ ቃል ይዞ በተለያየ ቀለም ማለትም በጥቁር ፣ በሰማያዊ ፣ በቀይ ቀለማት ዘመኑን በዋጀ ኅትመት (ወረቀት) ‹‹ይህ ጋዜጣችን የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን እምነትና ትምህርት ፣ ሥርዓትና ባሕል ፣ ታሪክና ዜና የሚያትም ስለሆነ ዜና ቤተ ክርስቲያን ተብሎ ተሠየመ›› ፡፡ ተብሎ እየታተመ እስከ አሁን ዘልቋል ፡፡ጋዜጣው ዋጋ ተተምኖለት በሽያጭ ለአንባብያን የሚሠራጭ እንደ መኾኑ መጠን በጥንቱ 0.10 የነበረ ሲኾን በየዘመናቱ የዋጋ ክለሳ እየተደረገበት በአሁኑ ወቅት ዋጋ ብር 40 ለውጭ ሀገር እጥፍ ይኾናል በሚል እየታተመ ይገኛል ፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልሣን ኾኖ የዘለቀው ዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ በብዙ ውጣ ውረድ አልፎ በአሁኑ ሰዓት 66ኛ ዓመት ቁጥር 167 ደርሷል፡፡ እነሆ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የሚዘጋጀው ይህ አንጋፋ ጋዜጣ ይዘቱን እና ኅትመቱን በማሳደግ ዘመኑን በዋጀ መልኩ ለትውልዱ ተደራሽ እንዲኾን እየሠራ ይገኛል፡፡
መምህር ማርቆስ ተበቃ ኬሬ
የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ



“በወንጌል ኮነ ሕይወትነ – በወንጌል ሕይወታችን ሆነ” በሚል መሪ ቃል የሚከበረው ፫ኛው ሀገር አቀፍ የስብከተ ወንጌል ቀን የመክፈቻ መርሐ ግብር ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አማካኝነት የተዘጋጀ ሲሆን
ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፪፻፲፰ ዓ.ም.)
ሚያዚያ ፲፭ ቀን ፳፻፲ወ፰ዓ.ም.
ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!