ማኀበራዊ ጉዳይ

የኢትዮጵያ ቤት ክርስቲያን ማኅበራዊ አስተዋጽኦ የሚመነጨው ከዐሥርቱ ሕግጋት እና ከስድሰተቱ ቃላተ ወንጌል ነው፡፡ ዐሠርቱ ቃላተ ኦሪት እና ስድስቱ ቃላተ ወንጌል በመተባበር ማኅበራዊ ሕግጋትን ያስተምራሉ፡፡

ማኅበራዊ ሕጎች በአንድ የኅብረተሰብ ክፍል ውስጥ የእረስ በእርስ ትስስር እና መተሳስብን ፍቅርንና አብሮ በሰላም የሚኖርበት አንድነትን የሚያጠብቁ መሠረቶች ናቸው፡፡ በመልካም መሠረት ላይ የሚኖር የኅብረተሰብ ክፍል ደግሞ በጊዜ ሂደት የራሱ የሆነ ባህል ይፈጥራል፡፡

ባህል ደግሞ የማንነቱ መገለጫ ከሌላ የኅብረተሰብ ክፍል የሚለይበት ኦርቶዶክሳዊ ማንነቱ የሚታወቅበት አንዱ መንገድ ነው፡፡ በዚህ መሠረት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚከተሉትን ማኅበራዊ አሰተዋጽኦዎች አድርጋለች እያደረገችም ነው፡፡

ማኅበራዊ አስተዋጽኦ

፩∙ በበጎ አድራጎት አገልግሎት መሳተፍ

የበጎ አድራጎት መነሻው ቅድሳት መጻሕፍት ሲሆኑ በኅብረተሰብ መካከል መተሳሰብን እና ሰብአዊ ርህራሄን ከማጎልበት ባሻገር ለነፍስ ዋጋ የሚያሰጡ ትምህርቶችንም የያዙ ናቸው፡፡

ስለሆነም የመንፈስዊ አገልግሎት ዋጋ ከመስጠቱም ባሻገር በህብረተሰቡ ዘንድ የመተሳሰብና የሰብአዊ ርኅራኄ መንፈስ ለማዳበር እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ የህንንም ለማድረግ ጠቃሚ የሆኑት ስልቶች ሕዝቡን ማስተማር፤ ማደራጀት፤ ማስተባበር እና ተቋማትን መክፈት ናቸው፡፡ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መነሻውም ሃይማኖት ነው፡፡
እግዚአብሔር ራሱ ያለምንም ከፍያ /በጸጋ/ ፍጥረትን ሁሉ መልካም መሆናቸውን እያረጋገጠ ከመፍጠር የዕለት ተዕለት ፈላጎታቸውን እሰከ መስጠት ድረስ መሠረት ሆአኖል፡፡ አምላካቸውን የተከተሉ ሰዎችም ከአምላካቸው ተምረው ይህንኑ የበጎ ፋቃድ አገልግሎት አበርክተዋል፡፡ አበ ብዙኀን አብርሃም ያለምንም ክፍያ መንገደኞችን ማብላቱንና ማጠጣቱ ዋና ማስረጃ ነው፡፡
በመጽሐፍ ቅድስ ውስጥ የተዘረዘሩ ብዙ አገልግሎቶች በበጎ ፈቃድ የተከናወኑ ናቸው፡፡ ሰው የተቸገረ ወገኑን እንዲሁም እንግዶችን እየተቀበለ በገንዘብ፣ በእውቀት፣ በጉልበት ያለውን ለሌለው መርዳትና ማገዝ ይጠበቅበታል፡፡ ደጉ ሳምራዊ ተጎድቶ፣ ቆስሎ ያየውን ሰው፤ ማንም ሳያስገድደው በፈቃዱ አንስቶ፤ ቁስሉን በዘይት ቀብቶ፤ ለሚረዱት ሌሎች ሰዎች ገንዘብ ሰጥቶ፤ ተመልሶ እንደሚረዳው ቃል ገብቶ መሄዱ የሚታወስ የቤተ ክርስቲያን ተግባር ነው፡፡ አሁንም በቤተ ክርስቲያን ካህናት፤ ዲያቆናት፤ ምእመናን ብዙ ነገሮችን በበጎ ፈቃድ የሠራሉ፡፡
የሕፃናት ማሳደጊያ እና የአረጋውያን መጦሪያ ተቋማት መከፈት

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲየን ድሆችን የመርዳት የቆየ ባህል አላት፡፡ ምጽዋት ከመሥዋዕት ይበልጣል እንዲል፡፡ /ማቴ ፱፥፲፩፤ሆሴ ፮፥፮፤ አረጋዊ መንፈሳዊ/፡፡ ብራብ አበልችሁኝ፤ ብጠማ አጠጣችሁኝ፤ ብታረዝ አለበሳችሁኝ፤ የሚለው የምጽዋት ዋጋ በቅዱስ መጽሐፍ፣ በብዙ ገድላትና ድርሳናት ጎልቶ ስለተሰበከ ምጽዋትን ለተቸገሩ መስጠት በጠቅላላ የኢትዮጵያውያን ታላቅ መንፈሳዊ እሴት ነው፡፡ ትናንትም ሆነ ዛሬ የማኅበረሰባችን ማኅበራዊ ዋስትና ይኸው ክርስቲያናዊ ባህላችን ነው፡፡ የቀድሞው፣ የዛሬውም የቆሎ ተማሪ የተማረው እና እየተማረ ያለው ቤተ ክርስቲያን በዘረጋችውና በሺሕ በሚቆጠሩ ዓመታት በዘለቀው በዚሁ ተቋም አካል ጽኑ ሃይማኖታዊ ባህል እንጂ በመንግሥት ወይም በሌሎች ድጋፍ አይደለም፡፡

በአጠቃለይ ቤተ ክርስቲያን ለተራቡት ቀለብ፣ ለታረዙት ልብስ፣ ለሕሙማን ፈውስ፣ ለአረጋውያን መጦሪያና ለእጓለምውታን ማሳደጊያ የሆነ ማኅበራዊ ዋስትና ለማረጋጥ በማስተባበር የተቻላትን ሁሉ ስታደርግ ቆይታለች፡፡

እነዚህ መኅበራዊ ተቋማት እንደዘመናችን ዓይነት መዋቅር ባይኖራቸውም በስንበቴና በጡት ልጅ እና በመሳሰሉት ማኅበራዊ መጠሪያዎች የሚታወቁ ማኅበራዊ ዋስትናዎች ነበሩ፡፡ ዘመናዊ የማኀበራዊ ዋስትና በኢትዮጵያ እሰከሚጀመርበት ድረስ ጧሪ የሌላቸው ሰዎች እና አሳዳጊ ያጡ ሕፃናት በዚህ መንገድ ሲረዱ ኑረዋል፡፡

እነዚህ ተቋማት ከተመሠረቱም በኋላ ቤተ ክትስቲያን አዲሶቹን ተቋማት መሥርታ የማኅበራዊ ዋስትና አገልግሎቷን አጠናክራ ቀጥላለች፡፡ በድርቅ ጊዜ ርዳታን በማስተባበር ስደተኞችን መርዳት ቤተ ክርስቲያን የተቸገሩትን መርዳት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ተግባሯ በመሆኑ ተግባሩን ስታከናውነው ኖራለች፡፡ ዛሬም በዘመናዊ መልክ ልማትና ተራድኦ ኮሚሽን በማቋቋም ድንገተኛ አደጋ ሲከሰት እህል ዘይት እና ሌሎች ምግቦችን በማቅረብ የሰብአዊ እርዳታና መልሶ ማቋቋም ተግባር አከናውናለች እያከናወነችም ትገኛለች፡፡

መንፈሳዊ ማኀበራትን መደራጀት

ለበጎ ፈቃድ አገልግሎት ምሳሌ የሚሆኑ ዝክሮች፣ ሰንበቴዎችና ማኅበሮች ወዘተ በስፋት ይገኛሉ፡፡ እነዚህ የተቀደሱና ጠናካራ ትውፊቶች የበጎ አገልግሎት ለመሰጠት አመቺ ናቸው፡፡ በገጠሩ አካባቢ በስፋት ይጠቀሙባቸዋል፡፡ በድንገት ሀብት ንብረቱ ቢቃጠልበት ርዳታ ያደርጉለታል፡፡ እንዲሁም ጧሪ ዘመድ ሳይኖረውና የሚሠራ ጉልበቱ ሲደክም ከቤታቸው በማስቀመጥ ተፈራርቀው የጦሩታል፡፡ ይህም ተግባር መጽሐፍ ቅድሳዊ ተግባር በመሆኑ በሕዝቡ አኗኗር ላይ በጎ ተጽዕኖ በማሳደሩ ለዚህ ድርጊት የቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ ክፍተኛ ነው ::

፪ መልካም ዜጋን በማፍራት

ሰው ሁሉ ለሚኖርባት ዓለም ነጻና ክቡር ዜጋ ነው፡፡ዜግነት የተፈጥሮ ሲሆን መልካም ዜግት ግን የመልም ጠባይና ምግባር ውጤት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እውነተኛና ቅድስት በመሆኗ ዜጎች ሁሉ በሃይማኖትና በምግባር ለሀገራቸውና ለሰማያዊት ርስታቸው መልካምና ታማኝ እንዲሆኑ ከማስተማርና ከመምከር የተቆጠበችበት አፍታ ጊዜ የለም፡፡ ምንም እንኳን በሥልጣኔ ስም የሚመጡ ጉዳዮች የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ከጊዜ ወደ ጊዜ ቢፈታተኑትም ቤተክርስቲያን ግን ከጥንት ጀምሮ ልጆቿ በሥነ ምግባር ታንጸው፣ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያደረባቸው የሀገርና የወገን አለኝታዎች እንዲሆኑ የተለያዩ ሥራዎችን ሠርታለች፡፡

፫ የሥራ ባህልን በማዳበር

ሥራ የኑሮ መሠረት መሆኑን ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡የምትመራባቸው ቅዱሳት መጻሕፍትም የሥራን ጠቃሚነት በስፋት የሚተነትኑና የሥራን ባህል የሚያዳብሩ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር አስቀድሞ ለአባታችን አዳም ገነትን ያበጃት ይጠብቃትም ዘንድ ሓላፊነትን ሰጥቶት ነበር፡፡ አዳም ከተሳሳተም በኋላ ጥሮ ግሮ በወዙ እንዲበላ፣ በስንፍና ተዘልሎ እንዳየቀመጥ፣ በወገኖቹ ላይ ጥገኛ ሆኖ እንዳይከብድባቸው ይልቁንም የድካሙን ፍሬ ቢመገብ መልካም እንደሚሆንለት ተነግሮታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህንን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት መሠረት በማድረግ ልጆቿ ዘወትር በሥራ የተጠመዱ እንዲሆኑ ይህ ካልሆነ ግን አእምሮአቸው የዲያብሎስ ተገዥ እንደሚሆን ታሰተምራለች፡፡ ከዚህ አኳያ ቤተ ክርስቲያን የሕዝቡን ሁለንተናዊ እድገት በማጽናት ለኢኮኖሚ ጤናማ እድገት፣ ለሕዝቡ ልማትና ደኅንነት መጠበቅ የበኩሏን ድረሻ እየተወጣች ነው፡፡

፬∙ሥነምግባርን በማሰተማር

ሥነምግባር የሚለው ቃል በሥራ ማማር፣ የሥራ መልካምነት ማለት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ክርሰቲያኖች በጎ ሥራን እንዲሠሩ፣ ሰዎችን ያለምንም ልዩነት እንዲወዱ፣ የራስን ሰውነት ሕይወትና ክብር ከሚጎዱ ዲርጊቶች እንዲረቁ ሕይወታቸውን በቅድስና መንፈሳቸውን በንጽሕና እዲያዙ ታሰተምራለች፡፡ ከዚህም ትምህርቷ የተነሣ ምእመኖቿ በጎ ሕሊና እንዲኖራቸው፣ ከአንደበታቸው መልካም ቃል እንዲወጣ ንግግራቸው ሁሉ ከቁጣና ከትዕቢት የራቀ ጠብን ከመጫር ይልቅ ሰላምና እርቅ አንድነት እንዲያወርድ ወደ እግዚአብሔር መቅረብና ከእርሱ ጋር ሊያኖር የሚችል መልካም ሥራን መሥራትን የሚፈልጉ እንዲሆኑ አድረጋለች፤ እያደረገችም ነው፡፡ በማኅበራዊ ሕይወትም የሌላውን ድካምና ስሕተት ለቅመው ከመክሰስና ከመተቸት ይልቅ ባለማወቅ ያጠፋነውን ወደ ማወቅ አድርሰው ያርሙታል፣ የደከመውን ያበረቱታል፡፡ ክፉውን ወደ መልካም ይለውጡታል፡፡ ሕይወታቸው በእግዚአብሔር ፊት ብቻ ሳይሆን በሰውም ፊት የተገለጠ ሰለሆነ በኅብረተሰቡም ፊት መልካም የሆነውን የፈጽማሉ፡፡ ‘’ስለምናገለግለው ስለዚህ ለጋስ ስጦታው ማነም እንዳይነቅፈን እንጠነቀቃለን በጌታ ፊት ብቻ ያይደለ  ነገር ግን በሰው ፊት ደግሞ መልካም የሆነውን እናስባለንና’’ ፡፡ በአጠቃለይ ቤተ ክርስቲያን ባላት የሥነ ምግባር ትምህርቷ ኅብረተሰቡ ለእግዚአብሔር እንዲሁም ለሀገሩና ለባልንጀራው ታማኝ እንዲሆንና ሓላፊነቱን፤ ተጠያቂነቱን በአግባቡ እንዲወጣ፤ ያለ እድልዎ ሥራን እንዲያከናውን በማሰተማር ሙስናን በመከላል ለሀገር ዕድገት አስተዋጽኦ ስታበረክት ቆይታለች እያበረከተችም ትገኛለች፡፡
ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ፤ ግብር ለሚገባው ግብርን ፤ቀረጥ ለሚገባው ቀረጥን ፤መፈራት ለሚገባው መፈራትን፣ ክብር ለሚገባው ክብርን ስጡ፡፡ በሚለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ መመሪያ መሠረት ቤተ ክርስቲያን የእንግዚአብሔር የሆነውን አሥራት በኩራት ለቤተክርሰቲያን ግብርን ደግሞ ለመንግሥት በወቅቱ እንዲከፍሉ ለማድረግ የማይናቅ ድርሻ ተወጥታለች፡፡ ይህን ማለት የሚያሰደፍረውም፡-
• አስተምህሮዋ አንዱ ለአንዱ እንዲታዘዝ፤ በትሕትና እንዲኖሩ ፈረሃ እግዚአብሔር እንዲኖረው ከሱስ ከባዕድ ተግባር ራሱን እንዲጠብቅ እና መልካም ዜጋ እንዲፈጠር የሚያደርግ በመሆኑ ነው፡፡
• ለረጅም ዘመናት በቄስ ትምህርት ቤት ትውልድን በመልካም ሥነ ምግባር የታነፀ ለሓላፊነት የሚበቃ እና ጠንካራ ዜጋ ለምድረግ ከሥር ኮትኩታ በማስደግ ያደረገችው እሰተዋኦም የሚዘነጋ አይደለም፡፡
• እሰከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የግብረ ገብ ትምህርት ከመደበኛ ትምህርት ጎን ለጎን እንዲሰጥና በሥነ ምግባር የታነጹ ዜጎች እንዲኖሩ ያደረገችው አሰተዋኦ  ከፍተኛ ነው፡፡
በተለይም በዚህ በዘመነ ሉላዊነት /Globalization/ በተለያየ መልኩ የሥነ ምብናር ችግር እየገጠመው ያለውን ትውልድ፣ በተሻለ መለኩ ለመቅረጽ መንግሥት በኮሚሽን ደረጃ አቋቁም የሚታገልበትን ሙስና ከሥሩ የሚነቅል ሥራ ለመሥራት ቤት ክርስቲያን ካለባት ሓላፊነት አኳያ እያደረገችው ያለው ትውልድን በሥነ ምብባር የማነጽ ሥራ የሃይማኖቱ ግዴታ እንደሆነ ያመለክታል፡፡

፭∙ በጤና ጥበቃ ዘርፍ በመሳተፍ

ጤና ማለት የበሽታ አለመኖር ብቻ ሳይሆን የአንድ ሰው /ማኅበረሰብ/፣ አካላዊ /physical/፣ ሥነ ልቡናዊ /psychological/ ማኀበረሰባዊ /social/ አእምሮአዊ /mental/ እና ሃይማኖታዊ ደኅንነት / Spritual wellbeing /  ነው፡፡ አስከፊ በሆነ ድህነትና ችግር ውስጥ ላለ ኅብረተሰብ የጤና ችግር ትልቁን ቦታ የሚይዝ ጉዳይ ነው፡፡ ይህም ከሥጋ ሕመም ባሻገር የሚፈጥረው የአእምሮ ጭንቀት የአንድ ኀብረተሰብ ክፍልን ምርታማነትና ውጤታማነት እጅጉን ይጎዳል፡፡ ቤተ ክፍስቲያን የጤናውን ችግር ለመቅረፍ ያላትን አስተዋጽኦ የሚከተሉትን መዘርዘር/መጥቀስ ይቻላል፡፡
• መንፈሳዊ እና ሥጋዊ ደኀንነትን በመስጠት
• አዕምሮአዊ ጤንነት እንዲኖር በማድረግ
• ሥነ ልቡናዊ ጤንነት በመስጠት
• ዘመናዊ ጤና ተቋማት ማስፋፋትና የመሳሰሉትን

፮∙ በትምህርት ዘርፍ

ባለአእምሮ ሰው በደማዊነት አእምሮው እያዘገመ እንዳይኖር በትምህርት ድንቁርናን አርቆ፣ ክፉና ደጉን ለይቶ በዕውቀት ዓለም እንዲኖር ልቡናን የሚያጠራና የሚወለውል፣ ማኅበራዊ ነጻነትን የሚጎናጽፍ ዕውቀት ማግኘት ያስፈልገዋል፡፡ ሥጋዊና መንፈሳዊ ዕውቀት በሰው ልጆች አእምሮ ተቀርጾ ማህበራዊ፣ ባህላዊ እና ኢኮኖሚዊ ሕይወታቸውን ጥበብ በተሞላበት የአኗኗር ዘይቤ እንዲመሩ የዕውቀት በር መክፈቻ ቁልፍ ነው፡፡
የዚህም ዓላማ፣
ጊዜውን የሚዋጅ ንቃተ ኅሊናው የዳበረ ትውልድ ወይም ዜጋ ለመፍጠር ከቄስ ትምህርት ቤት እስከ ከፍተኛ ተቋማት ሥርዓተ ትምህርትን መቅረጽ እና መረጃ መሳሪያዎች ማዘጋጀት የቤተ ክርስቲያን ተቀዳሚ ተግባር ሆኗል፡፡
ኢትዮጵያ ፊደልን ከነአገባቡ ይዛ የዓለም የራሳቸው ፊደላት ካሏቸው ጥቂት ሀገራት መካከል አንዷ ስትሆን መገለጫዋም የግእዝ ፊደላት ባለቤት መሆኗ ነው፡፡ በመሆኑም በተለያዩ ውጭ ሀገራት የግእዝ ትምህርት በፋኩልቲ ደረጃ መቋቋም ለጥናትና ምርምር ዓይነተኛ እገዛ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡
ዘመናዊ ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ከ1930ዎቹ በኋላ እንደ ትምህርት ሚኒስቴርነ ስታገለግል የቆየችው ቤተ ክርስቲያን የዘመናዊ ትምህርት ቤት በሀገራችን መስፋፋት ከጀመረበት ጊዜ በኋላም ቢሆን የራሷ ዘመናዊ ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ልጆችና ወጣቶች በሥነ ምግባር እየታነጹ፤ ለሕዝብና ለመንግስት የሚያገለግል አገር ወዳድ ዜጎችን በማፍራት በዘማናዊው ትምህርት ድርሻዋን እየተወጣች ትገኛለች፡፡

፯. ታረክን እና ጥበብን በመመዝገብ

ለኢትዮጵያ ሥነጽሑፍ መነሻው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ ብዙው ዓለም ገና የጽሕፈትን ጥበብ ገንዘብ ባላደረገበት ዘመን የቤተክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ከበግ፣ ከፍየልና ከልዩ ልዩ እንሰሳት ቆዳ ብራና ፍቀው፣ ቀለማትን በጥብጠው ብርዕ ቀርጸው የኢትዮጵያ ብሎም የውጭ ሀገራትን ታሪክ በመመዝገብ ለጥናትና ምርምር መነሻ ሆነዋል ማለት ይቻላል፡፡

፰.  የባህል አስተዋጽኦ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲን መሰረቷ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ የምትሰብከውም ሃይማኖትን ከትውፊት፣ ትውፊትን ከሥርዓት፣ ሥዓትን ከባህል ጋር በማቀናጅት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲን በሥነ ምግባር ትምህርቷ በኢትዮፕያ ውስጥ ለሚደረግ መልካም ባህሎች መነሻ ናት፡፡ በዚህ መሰረት ቤተ ክርስቲያን ያላትን ባህላዊ አስተዋ    ጽኦ ለመመልከት ያህል እንደሚከተለው ተዘርዝረዋል፡፡
• በአንድ ማዕድ የመመገብ ባህል /የአመጋገብ ሥርዓት/፣
• የአነጋገር ሥርዓት፣
• የእንግዳ ተቀባይነት ባህል፣
• አለባበስ/ ነጭ ልብስ፣ ወንድ የወንድን ሴት የሴት ወ.ዘ.ተ/፣
• ጋብቻን የማክበር ባህል
• የጀግንነት እና የሀገር ፍቅር ባህል፣
• ተከባበሮ የመኖር  እና የአብሮነት ባህል፣ ወዘተ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

መንፈሳዊ ትምህርት (ሥልጠና)

ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በቅዳሜ ገብረ እግዚአብሔር ሰማየ ወምድረ /በመጀመሪያ እግዚአብሔር አምላክ ሰማይንና ምድርን ከፈጠረ በኋላ በመጀመሪያው የሥነ ፍጥረት ቀን ቅዱሳን መላዕክትን ፈጥሮ ተሰወረባቸው መላዕክትም መኑ ፈጠርነ ወእምአይቴ መጻዕነ ማን ፈጠረን ከየትስ መጣን /ተገኘን / የሚለውን የምርምር ሐሳብ አንስተው ሲወያዩ አላዋቂ ዲያብሎስ ሁሉም ቅዱሳን መላዕክት በቦታ አቃማመጥ ከእርሱ በታች ሁነው ስለአያቸው እኔ ፈጠርኳችሁ አላቸው ቅዱሳን መላዕክትም በቦታ ከሆነ እኛ ከእኛ በታች የሆኑትን አልፈጠርንም በማለት የመመራመር ሥራቸውን ቀጥለው በአሉበት ሰዓት ሊቀ መላዕክት ቅ/ገብርኤል “ንቁም በበህላዌነ እስከ ንረክበ ለአምላክነ” ፈጣሪያችን አምላካችን እግዚአብሔርን እስከ ምናገኘው ድረስ ሁላችንም በተፈጠርንበት ሕልውና ፀንተን ልንኖር ይገባናል የሚለውን ትምህርት ለቅዱሳን መላዕክት በመንገሩ /በማስተማሩ/ የማረጋጊያ፣ የማጽናኛ ፣ ትምህርት ሰጥቷል ይህንን የማረጋጊያ ትምህርት በአግባቡና በጥልቀት ሰንመለከተው የመማር ማስተማር ሥራ የተጀመረበት ወቅት መሆኖን ቅዱሳን መጻሕፍትና ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያን ያረጋግጡልናል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ የሰው ዘር የሆነውን አዳምን በመልኩና በምሳሌው ከፈጠረ በኋላ ባለግዕዛን አእምሮ /ነጻ አእምሮ/ ሰጥቶ የማወቅ የመመራመር ጥበብንና እውቀትን ከመሰጠቱም ሌላ የሚበሉና የማይበሉ ዕጽዋትን ነግሮና አስተምሮ የማይበላው የተከላከለውን በልቶ ቢገኝ የሞት ሞት እደሚሞት አምላካችን በሰው ዘር ታሪክ የመፍጠርና የማስተማር ሥራውን በአዳም እንደ ጀመረ ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡

የአዳም ሦስተኛ ዙር የሆነውና እግዚአብሔርን በማገልገል የሚታወቀው ደገኛው ሰው ሄኖስ በሰማይ ላይ የተጻፈ ጽሁፍን አይቶና ተመልክቶ ዛሬ ለብዙ ቅዱሳት መጻሕፍት መጻፍና በዓለም ለሚገኙ ልዩ መጻሕፍትና የምርምር ሥራዎች መከናወን በዚያን ጊዜ ለነቢዩ ሄኖስ በደፍደፈ ሰማይ ተገልጦ የታየው ጽሁፍ እንደሆነ ታሪክ ይነግረናል፡፡ ምንም እንኳን ያ ዘመን ትምህርቱም ሆነ ታሪኩ የሚነገረውና የሚተረክው ጽሁፍ የማይከናወንበት የሕገ ልቡና ዘመን ቢሆንም የአጻጻፍ ሁኔታ /ጽሁፍ/ የተገለጠበት ጊዜና ወቅት ነበርና የጽሁፍ ትምህርት የተጀመረበት እንደሆነ ሊቃውንት በምርምር ሥራቸው ዘግበውት ይገኛል፡፡

ሰዎች በምድር ላይ እግዚአብሔርን መበደል በጀመሩበት ወቅት ጻድቁንና ንጹህ ሕሊና ያለውን ኖኅን አስነስቶ የበደሉ ሰዎችን አስተማሪ ትምህርቱን አልቀበል በማለት በደላቸው እየበዛ በሄደ ቁትር ኖኅና ልጆቹ የሚድኑበትን የጥበብና የእምነት ትምህርት ኖኅ ተምሮና ተመራምሮ ከእግዚአብሔር ቁጣና መቅሰፍት ራሱንና ቤተሰቡን አዳነ ከጥፋት ውሃ በሰላም ኖህ በተማረው ትምህርት ለእግዚአብሄር መስዋዕት አቀረበ የእግዚአብሔርን አዳኝነት ለልጆቹና ለቤተሰቡ አስተማሪ ከእግዚአብሔርም በረከትን አገኘ፡፡

የእውነተኛው ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ የሆነው አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሲመቱ ለመልከ ጼዴቅ ተብሎ የተነገረለት አባት እናት የትውልድም ዘመን የሌለው ለዘመኑ ጥንት ለሕይወቱም ፍፃሜ የሌለው መልከ ጼዴቅ ከእግዚአብሔር የተማረውንና በተሰጠው የሥልጣነ ካህናት ማዕረግ አብርሃምን እንዳሰተማረው እንደባረከውና አብርሃም ከአገኘው ሀብት ሁሉ ከአሥር አንዱን /አስራቱን/ ለእግዚአብሔር መስጠት እንዳለበት የነገረውና የሐዲስ ኪዳን መስዋዕት ምሳሌውን አብርሃም ያወቀውና የተማረው ከመልከ ጼዲቅ እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍና መተርጎማን ሊቃውንት ይነግሩናል፡፡

አበ ብዙኃን ተብሎ የተነገረለት አብርሃምም የእግዚአብሔርን ህልውና /መኖር/ ተመራምሮ የአወቀ ከመልከ ጼዲቅና ከእግዚአብሔር በአገኘው ትምህርትና በረከት ለልጆቹና ለተከታዮቹ ነገረ አስተማረ፡፡
ከዚህ በላይ ያለው አጭር ታሪክ ስንመለከት ሕገ ኦሪት መጻፍ እስከ ጀመረበት ጊዜ ብዙ ቅዱሳን አበው ከእግዚአብሔር በአገኙት ጥበብና ዕውቀት ተምረውና ተመራምረው ከመዝ ይቤ እግዚአብሔር እግዚአብሔር እንዲህ ይላል እያሉ ሕዝቡን ያስተምሩ ነበር፡፡

እግዚአብሔርን ብቻ እንዲያመልኩ ከእርሱ በስተቀር ሌላ አምላክ እንደሌለ የአስተማሩበትና ዘመኑም ሕግ ያልተጻፈበት በሕገ ልቡና እግዚአብሔርን አውቀውና አዳኝነቱንም ተረድተው ያአስተማሩበት እንደሆነ የታሪክ ሂደት ያስረዳናል፡፡ ይህን ታሪክ ስንመለከት በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን ዘመን ለተነሱት ታላላቅ ቅዱሳን ነቢያት ሐዋርያት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የትምህርትና የምርምር ሥራዎቻቸው ዋና መነሻ ታሪክ እንዲሆን ተረድተናል /እንረዳለን/፡፡

የመንፈሳዊ ትምህርት አሰጣጥ

በሕገ ኦሪት

እግዚአብሔር አምላክ ለሙሴ የእምነት ሕግንና ሥርዓትን አስተምሮ ሰጠው ለልጆቹም ሆነ ለሕዝበ እስራኤል የሚያስተምርበትን የሕግ መጽሐፍ ጽፎ እንዲይዘውና እንዲያስተምር ታዘዘ በተለይም በዘዳግም ምዕራፍ 6፡4-9 ያለውን ኃይለ ቃል ስንመለከተው የመማር ማስተማር ሥራና ተግባር በቃልም በጽሁፍም የተጀመረበትና የተከናወነበት ጊዜ እንደነበር ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡ ቃሉም “እስራኤል ሆይ ስማ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው አንተም አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም  ዛሬ አንተን የማዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ፡፡

ለልጆችህም አስተምረው፣ በቤትህም ስትቀመጥ በመንገድም ስትሄድ፣ ስትተኛም ስትነሳም ተጫወተው፣ በእጅህም ምልክት አድርገህ እሰረው በአይኖችህም መካከል እንደክታብ ይሁንልህ በቤትህም መቃኖች በደጃፍህም በሮች ላይ ጻፈው”፡፡ በማለት እግዚአብሔር አምላክ ለሙሴ እንዳሰተማረውና ሙሴም የተማረውን ትምህርትና የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለልጆቹና ለሕዝብ እስራኤል በትጋት ፣ በቅንነትና ፍጽም በሆነ ፍቅር አስተማረ 5ቱን የሙሴ መጽሐፍ ተብለው የሚነገርላቸውን ሕገ ኦሪትም ኦሪትም ለትውልድ በማስተላለፍ እስከ አሁን ድረስ እንማርበታለን ዘመኑም 3500 ዓመት እንደሆነው ከቅዱስ መጽሐፍ ታሪክ እንረዳለን /ከሙሴ እስከ አሁን ያለው ዘመን)
እግዚአብሔር አምላክ ክህነትን ከምስፍና ጋር አጣምሮ የያዘውን ሙሴን የሚረዳና የክህነት አገልግሎትንም ከምስፍና ለመለየት ስለፈለገ ወንድሙን አሮንን ካህን አድርጎ እንዲሾመው ካህኑ አሮንንም የሙሴ አፈ ጉባኤ /አፈ መምህር/ ሁኖ የክህነት አገልግሎትን እርሱና ልጆቹ ተሾመ የማስተማር ሥራ ወይም ቀጥሎ አስተማሪ /ዘጸ 28፡1 ፣ 29፡1/ የአሮንን ፈለግ በመከተል ሌዋውያኑ የማስተማር ስራቸውን አስተምረዋል፡፡

የክህነት አገልግሎትንም ሰጥተዋል፡፡ ሌላው በዘመነ መሳፍንትና ዘመነ ንግስታት የተነሱት ካህናትና ነቢያት ስለእግዚአብሔር ሕልውና ሳያፍሩና ሳይፈሩ አስተምረዋል፡፡ ሕዝቡ በምክረ ካህን ፣ በፍቃደ ካህን እንዲጓዝ ምክርና ተግሳጽ ሰጥተዋል ከእነዚህም በዋናነት የሚጠቀሱት ኢያሱ፣ ዳዊት፣ ሰሎሞን፣ ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ፣ ሕዝቅኤል ዳንኤልና ሌሎችም ነቢያት የማስተማር ሥራቸውን በብቃትና በንቃት ተወጥተዋል ታላቁንና የመጨረሻውን የክብር አክሊል ከፈጣሪያቸው ተሸልመዋል፡፡

የመንፈሳዊ ትምህርት አሰጣጥ በአዲስ ኪዳን

በብሉይና በአዲስ ኪዳን መካከል የነበረው መጥምቀ መለኮት ቅድስ ዮሐንስ “ነስሑ ወእመኑ እስመ ቀርብት ይእቲ መንግስተ ሰማት” መንግስት ሰማት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ እያለ ያስተምር እንደነበረ የንስሐ ጥምቀትም ያጠምቅ እደነበረ ብዙ ተከታይ ተማሪዎችም እንደነበሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ይነግረናል፡፡ /ማቲ 3፡2 ፣11፡2/

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው 12 ዓመት በሆነው ጊዜ በኢየሩሳሌም ከበነበሩ መምህራን መካከል ተገኝቶ እንደተማረና ለመምህራኑም ልዩ ልዩ ጥያቄ እንዳቀረበላቸው በመልስና ከቃሉ ንግግር ማማር የተነሳ የሰሙትና ይገረሙ እንደነበር ከቅዱስ ቃሉ መረዳት ይቻላል /ሉቃ 2፡46/

ከዚህም በተጨማሪ ጌታችን መድኃኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና ይግባውና እንደ አምላክነቱ ሳይሆን እንደ ሰውነቱ ቀስ በቀስ በሚያድግበት ወቅት ዕድሜው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ ትምህርት ቤት ገብቶ እንደተማረ መምህራኑ በሚያስተምሩት ጊዜ ልዩ ልዩ ጥያቄ ያቀርብ እደነበርና የተግባረ ዕድ ሥራንም መምህራኑን ይረዳቸው እንደነበር በተአምረ ኢየሱስ ተጠቅሶ /ተጽፎ/ ይገኛል፡፡

ከዚህም ጋር ተያይዞ በመዋዕለ ሥጋዌው 30 ዓመት ሲሞላው ተጠምቆ ገዳመ ቆሮንጦስ ገብቶ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከጾመ በኋላ የማስተማር ሥራውን ጀመረ ደቀ መዛሙርቱንም ከተለያዩ ተግባረ ሥራ ለወንጌል አገልግሎት መረጠ /ማሬ 4፡17/ 12ቱን ሐዋርያት ደቀ መዛሙርት መርጦና አስተምሮ ሙሉ ሥልጣንም ሰጥቶ በዓለም ዙሪያ ወንጌልን እንዲያስተምሩ ከተሟላ የእምነት ትጥቅ ጋር ተላኩ /ማቴ 10፡1-42/
በመቀጠልም በድንቁርና ዓለም ውስጥ ያለው የሰው ዘር ያውቅ ይረዳና ይማር ዘንድ ሌሎችን ሰባ መምህራንን መርጦ አሰልጥኖና ባለሙሉ ሥልጣን አድርጎ አልጫ የሆነውን ዓለም በትምህርት ጨው እንዲያጣፍጡ ሾማቸው /ሉቃስ 10፡1/

በአጠቃላይ በ3 ዓመት ከ3ወር ውስጥ ዓለምን ዞረው የሚስተምሩ ደቀ መዛሙርትን መርጦና ሹሞከመላኩም ሌላ የ5 ገበያ ከ5,000 ሕዝብ በላይ ይከተለው እንደነበር ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል ከዚህ ላይ መርዳትና መናገር የምንችለው የመማር ማስተማር ሥራ ቀደም ሲል የነበሩት መምህራን ነቢያት የጀመሩትና ያስተማሩ ቢሆንም የህግና የሥርዓት ጀማሪውና ፈጸሜው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመማርንና የማስተማርን ጥቅም የሰው ልጅ አውቆና ተረድቶ እንዲማር ራሱ ለሰው ልጆች አርአያ ምሳሌ ለመሆን የጥበብና የዕውቀት ምንጭና ፈጣሪ ቢሆንም እንደሰውነቱ ትምህርት ቤት ገብቶ ተምሮአል አስተምሮአል ባለሙሉ ሥልጣን አድርጎ ሐዋርያትን ሰባ ሁለቱን ደቀ መዘሙርት መርጦ የሰማይና የምድር ስልጣን ሰጥቶ ስለላካቸው ዓለምን በ4 ማዕዘን ዙረው አስተማሩ።

የነቢያትንና የሐዋርያትን ፈለግ በመከተል ብዙዎች መምህራን ሊቀውተ ቤተ ክርስቲያን የማስተማር ጠቀሜታን አውቀውና ተረድተው ዋጋቸው ከልዑል እግዚአብሔር ለመቀበል ራሳቸውን መስዋዕት አድርገው አስተምረዋል መክረዋል ፡፡

ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመንፈሳዊው የትምህርት አሰጣጥ እንዴት እንደነበር በአጭሩ ስንመለከተው በቀዳማዊው ምንሊክ ዘመን /በ900 ዓመተ ዓለም አካባቢ/ ጽላተ ሙሴና ሰባው ለቃውንት /የብሉይ ኪዳን መምህራን/ ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው በፊት ሀገራችን ኢትዮጵያን በፈጣሪ  የምታምንና ሕገ እግዚአብሔርን የምታስተምር እደነበረች ታሪክ ቢነግረንም የሕገ ኦሪት ትምህርት መስፋፋትና መጠናከር የጀመረው ከቀዳማዊ ምንሊክ ከታቦተ ሙሴ መግባትና በሊቀ ካህናቱ አዛርያስ መሪነት የሰባው ሊቃውንቱ  ወደ ሀገራች መምጣት ከእነርሱም ጋር የመጡት መጻህፍተ ብሉያት መገኘት ሲሆን የክርስቶስንና የሐዋርትን አስተምሮ ተከትሎ በ34 ዓ.ም ጥቅምት ወደ ሀገራችን በኢትዮጵያው ጀንደረባ አማካኝነት መግባት /የሐ.ሥራ 8፡26-40 / በመቀጠልም በ4ኛው ክፍለ ዘመን በአብርሃና አጽብሃ ዘመነ መንግስት በከሳቴ ብርሃን አባ ሰላማ አማካኝነት የሀዲስ ኪዳን እምነትና ሥርዓትን ተቀብላ ዲያቆናትን፤ቀሳውስትን፤ መምህራን፤ በማስተማርና ሥልጣነ ክህነትን በመስጠት ቤተ ክርስቲያን እንድትሰፉና እንድትስፋፋ ሆነች፡፡

አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናትም እንዲሠሩ ሆነ በመቀጠልም በ5ኛ ክፍለ ዘመን የ9ኑ ቅዱሳን ወደ ሀገራችን መግባትና ገዳማትን መመሥረትና ማስተማር የቤተ ክርስቲያን መጠናከሪያ የወንጌል ማስተማር ሥራ በመስፋፋት ላይ እደነበር ከቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለመረዳት ይቻላል፡፡

ጠቅለል ለማድረግ የትምህርትና የሌሎችንም የሥራ ዘር ማዕከል የነበረችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአሠራር መላላት፣ የተጠናከረ የአደረጃጀት ሥልትና ዘዴ ያለመኖር፣ የእኔነት ስሜትና ፈላጎት ያለመኖር ይሁን ወይም ባልታወቀ ምክንያት የመንፈስ ቅዱስ ብርሃን በልዩ መልክ ያበራላትና የተቀደሰ ተግባሯንና ዓላማዋን በልዩ የመንፈስ ቅዱስ ምርጫ ታከናውንና ታስተምር የነበረችው ቤተ ክርስቲያን የመማር ማስተማሩ ሥራ ቀዝቅዞ ይታያልና በከፍተኛ ሁኔታ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት አደረጃጀቱም ሆነ አሠራሩ የቤተ ክርስቲኒቱ አስተምህሮ እንዳለ ሆኖ ዘመኑ በሚፈቅደው መልኩ ለሁሉም የቤተ ክርስቲያኒቱ ልዩ ልዩ ሠራተኞች የተለያዩ ሥልጠናዎችን በመስጠትና ሠራተኞችን በማብቃት እንደ አባቶቻችን ለቤተ ክስቲያን ብዙ ሥራ መስራት ይቻላል ፡፡

የቅዱሳን ሕይወት(ክብረ ቅዱሳን)

በሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገብረአማኑኤል

ቅድስና በምንልበት ጊዜ ቅድስናን በሁለት ከፍሎ ማየት ተገቢ ይሆናል፤ ይኸውም፡-
• ሀ. የባሕርይ ቅድስና ፤
• ለ. የጸጋ ቅድስና ማለት ሲሆን የባሕርይ ቅድስና በምንልበት ጊዜ ለእግዚአብሔር ብቻ የምንገልጸው ልዩ አገላለጽ ነው፡፡ የጸጋ ቅድስና በምንልበት ጊዜ ደግሞ ሰማያውያን መላዕክትና ምድራውያን ሰዎች ራሳቸውን ለቅድስና አዘጋጅተው ሲገኙ ቅድስናውን የሚያገኙት የቅድስና ባለቤት ከሆነው ከእግዚአብሔር የሚገኝ ልዩ ስጦታ ነው፡፡ በተለይ ምድራውያን ሰዎች በሃይማኖት ጸንተው፤ በበጎ ሥራ ተቃኝተው በቅን ልቡና አግዚአብሔርን ሲያገለግሉ ቅዱሳን ይሆናሉ፤ ቅዱሳንም ይባላሉ፡፡ ‹‹እኔ አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ›› ተብሏልና፡፡ (ዘሌ 19፡2)

የኢትዮጽያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን በምንልበትም ጊዜ ብሔራዉያን ቅዱሳንንና ከዉጪ ወደ ኢትዮጽያ መጥተዉ ያበረከቱትን ከፍተኛ መንፈሳዊ አገልግሎት ከግምት ዉስጥ በማስገባት የኢትዮጽያ ቤተ ክርስቲያን ቅድስናን ሰጥታ፣ በየስማቸዉ ቤተ ክርስቲያን አንፃ፣ ፅላት ቀርጻ፣ ገዳም ገድማ ያከበረቻቸዉና የምታስከብራቸዉ ቅዱሳን በርካታዎች ሲሆኑ በዚህ ፅሁፍ አጠቃሎ መግለጽ ባይቻልም ለግንዛቤ ያህል የአገር ዉስጥና የዉጭ ሀገር ቅዱሳን በማለት በሁለት ዐበይት ክፍሎች ከፍሎ መግለፅ ይቻላል፡፡

ይሁን እንጂ ከላይ እንደተገለፀዉ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸዉን ፈፅመዉ ዘለዓለማዊ ዕረፍታቸዉን በኢትዮጽያ ምድር በማድረጋቸዉ ብሔረ ሙላዳታቸዉን ለመግለፅ ያህል ታስቦ የተገለፀ ጽሑፍ መሆኑ ከግንዛቤ ዉስጥ መግባት ይኖርበታል፡፡

የኢትዮጽያን የሁለት ሺህ ዘመን ቅዱሳን ታሪክ በዚህ ጽሑፍ አምልቶና አስፍቶ መግለፅ ባይቻልም ዝርዝር ታሪኩን ለታሪክ ጸሐፊዎች በመተዉ የኢትዮጽያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ አለኝታ የሆኑትን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ዐበይት መምህራንን፣ እንደዚሁም በቤተ ክርስቲያናችን ስም በየአረፍተ ዘመናቱ መላ ሕይወታቸዉን የሰዉ ዘር የሆነዉን ሁሉ በሥራና በጸሎት በማገልገል፣ እግዚአብሔርን በማመስገን ሕይወታቸዉን መሥዋዕት አድርገዉ ያቀረቡትንና እጅግ በጣም ከፍተኛ የሆነዉን ገድል የፈጸሙትን ሁሉ ቤተክርስቲያናችን የጾታ ልዩነትን ሳታደርግ በገድላቸዉ ጽናትና በትሩፋታቸዉ ብዛት ብፁዕና ብፅዕት፣ ቅዱስና ቅድስት ሊያሰኝ ከሚችል የብፅዕናና ቅድስና ማዕረግ የደረሱ መሆናቸዉን በማረጋገጥና በስማቸዉም ቤተክርስቲያን እንዲታነጽ፣ ገዳም እንዲገደም፣ ደብር እንዲደበር፣ ገድልና ድርሳን እንዲጻፍላቸዉ፣ ወርሃዊና ዐመታዊ በዓላቸዉ እንዲታሰብና እንዲዘከር በማድረግ በቅዱስነት ያወቀቻቸዉንና ያሳወቀቻቸዉን ኢትዮጰያዉያንና ብሔረሙላዳታቸዉ ከኢትዮጰያ ዉጪ የሆኑትን ቅዱሳንና ቅዱሳትን ስም ዝረዝር በከፊልም ቢሆን እንደሚከተለዉ ለመግለጽ እንሞክራለን፡፡

ኢትዮጰያዉያን ቅዱሳንና ቅዱሳት

1. ሕጽዋ ለሕንደኬ ንግስተ ኢትዮጰያ

የክርስትና እምነት ወደ ኢትዮጰያ የገባዉ ወይም ኢትዮጰያና የክርስትና ሐይማኖት የተዋወቁት ሐዋርያዉ ቅዱስ ሉቃስ በግብረ ሐዋርያት 8፡26-40 ላይ እንደመዘገበው ጃንደረባው እንደ ብሉይ ኪዳን ሥርዓት ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዞ ሥርዓተ አምልኮትን ፈጽሞ በፍኖተ ጋዛ ሐዋርያው ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን ጃንደረባ ባጠመቀው ጊዜ ነው፡፡ ዘመኑም ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ34 ዓ.ም. ነው፡፡
‹‹የቤተ ክርስቲያን አባት›› እየተባለ የሚጠራው አውሳብዮስ የወንጌላዊው ሉቃስን ግብረ ሐዋርያት መሠረት አድረጎ ‹‹ሕጽው ለወገኖቹ ሆነ የኢትዮጵያ ሐዋርያ እሱ ነው›› በማለት ጽፎአል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ገጽ 18 ላይ ይመለከቱ፡፡

2. ቅዱሳን ነገስታት አብርሃ ወአጽብሓ

አብርሃ ወአጽብሓ የተሰኙ ቅዱሳን ነገስታት(ወንድማማቾች) እንደ አንድ ልብ መካሪ፤ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ በመሆን ፍጹም በሆነ ስምምነት ለ15 ዓመታት ያህል ኢትዮጵያን በጋራ ከአስተዳደሩ በኋላ እንደ አበው ሐዋርያት ዕጣ ተጣጥለው አብርሃ በአክሱም፤ አጽብሓ በሸዋ መናገሻ ከተማውን ኤረር በማድረግ መንበረ መንግሥታቸውን ዘርግተው እየተመካከሩ ኢትዮጵያን በማስተዳደራቸው፤ ለሀገሪቱና ለቤተ ክርስቲያን ያደረጉትን ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከግምት ውስጥ በማስገባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለሁለቱ ወንድማማች ነገሥታት የቅድስና ማዕረግ ሰጥታቸዋለች፡፡ በስማቸውም ቤተ ክርስቲያን አንጻለች፡፡ ወርኀዊና ዓመታዊ በዓላቸውንም በየዓመቱ ጥቅምት 4 ቀን እንዲታሰብና እንዲከበርም አድርጋለች፡፡ (ታሪከ ነገሥት አብርሓ ወአጽብሓ ከመምህር ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ 1989 ዓ.ም አዲስ አበባ)

3. አፄ ካሌብ

ከአብርሃና አጽብሓ ቀጥሎ ከተነሡት ቅዱሳን ነገሥታት ክርስትናን በማስፋፋትና በመንከባከብ ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ያደረጉት ከ485-515 ዓ.ም. የነበሩት አፄ ካሌብ ናቸው፡፡
አፄ ካሌብ ስለ ክርስትና መስፋፋት፤ ስለ ክርስቲያኖች አንድነት ብዙ ተጋድሎን ከተጋደሉና ከአሳለፉ በኋላ መንግሥታአውን ለልጃቸው ለአፄ ገብረ መስቀል አስረክበው፤ መንነው፤ ልብሰ ምንኩስናን ለብሰው ከአክሱም ወደ ሰሜን ምሠራቅ በሚገኘው በአባ ጰንጠሌዎን ገዳም በሚገኘው ዋሻ የምናኔ ሥራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ከዚህም ጋር ቤተ መንግሥታቸውን ለቀው በመነኑበት ሰዓት እጅግ በጣም ከፍተኛ የሆነውን ማለትም የነገሡበትን ዘውድ ወደ ጌታ መቃብር ጎልጎታ ልከው በምናኔ 12 ዓመታት ከተጋደሉ በኋላ በ536 ዓ.ም. ግንቦት 20 ቀን አርፈዋል፡፡ አፄ ካሌብ በምንኩስናና በምናኔ ሕይወት የቅዱሳንን አሠረ ጽድቅ ፈጽመው ያለፉ ደገኛ ንጉሥ ስለነበሩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቁጥራቸው ከቅዱሳን ነው፡፡ (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ 1974 ዓ.ም.)

4. አባ ዮሐኒ

አባ ዮሐኒ ብሔረ ሙላዳችው በክልል ትግራይ፤ በተንቤን ልዩ ስሙ ሀገረ ሰላም ከተባለው ቀበሌ ሲሆን የነበሩበትም ዘመን በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ነው፡፡ በቆላ ተንቤን ደብረ አንሣ(ዓሣ) ከተባለው በረሓ በጾምና በጸሎት ተወስነው ይኖሩ ከነበሩት ከአባ አሞኒ ጋር እንደ ኖሩ፤ ዕድገታቸውም በእናት ጡት ሳይሆን ቶራ እያጠባች እንዳሳደገቻቸው በገድለ አቡነ ዮሐኒ ተመዝግቧል፡፡ ገዳማቸውም ደብረ አንሣ(ዓሣ) ተብሎ የተሰየመ ሲሆን ወርኀዊና ዓመታዊ በዓላቸውም ህዳር 5 ቀን ይታሰባል፡፡ ( ምንጭ፡- 1. የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ከዶ/ር ሥርግው ሐብለ ሥላሴ 2. Journal of Ethiopian Studies. Vol 3 No. 2 July 1975)

5. ቅድስ ያሬድ

ቅዱስ ያሬድ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ505 ዓ.ም. የተነሣ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዓለም በሚታወቅበት ሙያውና ዕውቀቱ በመንፈስ ቅዱስ የተቃኘ የመንፈሳዊ ዜማ ደራሲ የቅኔ ተመራማሪ፤ ኪሩቤልን በሚያስምስለው ጣዕመ ዝማሬ የተወደደና ድምፅ መልካ ማሕሌትዊ ነው፡፡
ቅዱስ ያሬድ ድጓ፤ ዝማሬ መዋሥእትና ምዕራፍ የተሰኙ የዜማ መጻሕፍት አሉት፤ የብሉያት የሐዲሳትና የሊቃውንት መጻሕፍት ትርጓሜም ሊቅ ነው፡፡ እነዚህ ከብሉያት ከሐዲሳት ከሊቃውንት መጻሐፍት ለጸሎትና ለማሕሌት የሚስማሙትን ቃላት እየመረጠ ምሥጢራትን ከትርጓሜ እያስማማ ዜማዎቹን በዐራቱ ክፍላተ ዘመን በመፀው፤ በሐጋይ፤ በጸደይና በክረምት በመክፈል የየወቅቱን የተፈጥሮ ሥነ ባሕርይ በአንክሮና በምስጋና በሚገልጽ ጣዕም እንዲዘምሩና እንዲጸልዩ ያደረገ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ደራሲ ነው፡፡ ዜማውንም ግዕዝ፤ ዕዝል አራራይ በሚል በሦስት የዜማ ስልት ከፍሎ ዘምሮታል፡፡
ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የዜማ ድርሰቱን ያዘጋጀው ከ540-560 ዓ.ም. ባለው ዘመን ነው፡፡ ማሕሌታዊው ቅዱስ ያሬድ በኢትዮጵያ ሰሜናዊ ክፍሎች ለ11 ዓመታት እየተዛዋወረ ሲያስተምር ቤተ ክርስቲያንን ያገለግልና ሲያስገለግል ቆይቷል፡፡

በመጨረሻም በሰሜን ተራራዎች ሥር ካሉት ገዳማት በአንዱ ዋሻ ውስጥ ገብቶ በጾም፤ በጸሎት፤ በብሕትውና ዘመኑን አሳልፎአል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ እስከ ዛሬ እልፈትና ውላጤ ያላገኘው በጣዕመ ዝማሬው በምልክቱ ልዩ የሆነ የዜማ ድርሰቱን ለኢትዮጰያ ቤተ ከርስቲያን ያበረከተ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሊቅ በመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዝክረ ስሙን በጥንቃቄ ጠብቃ፤ በስሙ ጽላት ቀርፃ፤ ቤተ ክርስቲያንን አንጻ፤ ገድሉን ጽፋ በዓለ ዕረፍቱን በየዓመቱ ግንቦት 11 ቀን ታከብራለች፡፡ (ምንጭ፡- The Ethiopian Orthodox Tewahedo Church Faith, order of worship and Ecumenical relations, July 1996)

6. ሌሎች

• ቅዱስ ይምርሃነ ክርሰቶስ
• ቅዱስ ሐርቤ(ገ/ማርያም)
• ቅዱስ ላሊበላ
• ቅዱስ ነአኩቶ ለአብ

እነዚህ ቅዱሳን የነበሩበት ዘመን ከ11ኛው እስከ 12ኛው ክፍለ ዘመን ሲሆን ምስፍንናን ከክህነት፤ ክህነትን ከምንፍስና ጋር አስተባብረው በመያዝ ለክርስትና መስፋፋት፤ ለቤተ ከርስቲያን ዕድገት፤ ለአገር አንድነት የከፈሉት መስዋዕትነት፤ ያቆዩት መንፈሳዊ ቅርስ በዐይን የሚታይ በእጅ የሚዳሰስ ከመሆኑም በላይ ለሀገር ኢኮኖሚ የደም ሥርና የጀርባ አጥንት ሆነው የሚታዩት ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ሕያው ምስክሮች ናቸው፡፡ በመሆኑም እናት ቤተ ክርስቲያን ከላይ ስማቸው ለተጠቀሱው መንፈሳውያን ነገሥታት የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ፤ ገድላቸውን ጽፋ ለትውልደ ትውልድ አቆይታለች፡፡
(ምንጭ፡- 1. የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትናንትና ዛሬ መስከረም 1990 ዓ.ም 2. ዜና መዋዕል ዘብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ነሐሴ 1978 ዓ.ም. 3. የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ከዶ/ር ሥርግው ሐብል ሥላሴ 1981 ዓ.ም.)

ነገረ መለኮት (Theology)

<<Theology >> የሚለው ቃል ከሁለት የግሪክ ቃላት ማለትም ‹‹Theo›› እና ‹‹logy›› የተወሰደ ሲሆን ትርጓሜውም ‹‹ Theo›› ማለት ‹‹God›› ማለት ሲሆን ‹‹logy›› ደግሞ study or knowledge የሚል ቀጥተኛ ትርጉም አለው፡፡ በመሆኑም ‹‹Theology›› (የነገረ መለኮት) ማለት ስለ እግዚአብሔር የማይጨበጠውን፣የማይላጠውን፣ የማይገመተውን እንዲሁም ከሰዎች አእምሮ በላይ የሆነውን ጌትነቱንና አምላክነቱን መንፈስ ቅዱስ በገለጠላቸው መጠን ሰዎች የሚረዱበት ጥበብ ነው፡፡

እግዚአብሔር ተብሎ ወደ ግዕዝ የተተረጉመው በዕብራይስጡ ቋንቋ ኤል ወይም በብዙ ቁጥር ኤሎሄም የሚለው ቃል ነው፡፡ ኤል ማለት  ኃይል ማለት ነው፡፡ በታላቁ መጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ ሌሎች የእግዚአብሐር ስሞችም ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ ያህዌ ማለት የነበረ ያለና የሚኖር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚለው የግዕዝ ቃል ወደ አማርኛው ሲተረጎም የሀገር  ወይም የዓለም ጌታ ማለት ነው፡፡

በምድራችን ላይ በርካታ ሃይማኖቶች፤ እምነቶችና አመለካከቶች የመኖራቸውን ያህል ፍጥረታትን ሁሉ የፈጠረና (ያስገኘ) እና የየዕለት ሁኔታዎችን  የሚመራ እና  የሚቆጣጠር አንድ ከሰዎች በላይ የሆነ የማይታይ ትልቅ ኃይል ያለ መሆኑን አብዛኛው ወገኖች ይስማማሉ፡፡ ይሁን እንጂ እያንዳንዱ ሃይማኖት የራሱ የሆነ መመሪያና ትምህርት አለው፡፡

በዚህ መሰረት የክርስትና ነገረ መለኮት  ስንል ስለ እግዚአብሔር ህልውና ስለጠባዮቹ ስለመለኮታዊ አንድነቱ ሶስትነቱ ለፍጥረቱ ስለሚያደርገው ጥበቃ (መግበቱ) ከሶስቱ አካላት አንዱ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ሰው ሆኖ ዓለምን ማዳኑንና በአጠቃላይም ለዚህ ሁሉ ትምህርት ምንጭ በሆነው አምላካዊ መጽሀፍ የተገለጸው ሃይማኖታዊ ሥርዓት የሚመረምር ትምህርት (ዕውቀት) ማለታችን ነው፡፡

መሆኑም በዚህች አጭር ፅሁፍ ውስጥ ይህንን ሀሳብ በስፋት ለማየት አባይን በጭልፋ ያህል ከባድ ስለሆነ በነገረ መለኮት ትምህርት ውስጥ በተለይ በኢትዮጵያ ኦርዶቶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ያለውን አስተምሮ በአጭሩ ለማየት እንሞክራለን፡፡

ሀልወተ እግዚአብሔር
ለእግዚአብሔር ህላዌ ማስረጃነት ከሚቀርቡት በርካታ ጉዳዮች መካከል በተለይ የፍጥረታት ሥነ ሥርዓትና አሠራሩ፣ የህሊና ምስክርነት ፣የሠው ልጆች የተፈጥሮ ዝንባሌ፣ የቃለ እግዚአብሄር፣ የታሪክ ምስክርነት ወዘተ….. ይገኙበታል፡፡

ቅዱስ መጽሐፍ ወፎችንና እንስሳትን ብትጠይቋቸው ብዙ ሊያስተምሯችሁ በቻሉ ነበር፡፡ በምድር ላይ እና በባህር ውስጥ የሚኖሩትን ፍጥረቶች ጥበብ እንዲያስተምሯችሁ ብትጠይቋቸው ሁሉም እግዚአብሔር አንደሰራቸው ያስረዱአችኋል፡፡ የፍጥረቶቹን ሕይወት የሚመራ እግዚአብሔር ነው፡፡ የእያንዳንዱ ሰው ነፍስ በእግዚአብሔር ሥልጣን ስር ነው፡፡›› (መ.ኢዮ 12÷7-10) በማለት ዓለምን ያስገኘ እግዚአብሔር መሆኑን በግልጽ ያስተምራል፡፡ መዝሙረኛው ቅ/ዳዊትም ይህንን ሀሳብ ሲያጠናክረው ‹‹ሰማያት የእግዚአብሔር ክብር ይናገራሉ፣ የሰማይ ጠፈሮችም የእግዚአብሔር ሥራ ያውጃሉ፡፡›› (መዝ19፡1) በማት ከእግዚአብሔር ውጭ ይህች ዓለም ሌላ አዛዥና ባለቤት እንደሌላት ምስክርነቱን አስቀምጧል፡፡

በአንድ ወቅት በአቴና ከተማ የሚኖሩ ሰዎች ስለ እግዚአብሄር ሀልወት ለማመንና ለመቀበል ተቸግረው መስዋዕት እያቀረቡ መስዋዕት የሚያቀርቡለትን አምላክ ባለማወቃቸው ‹‹ ለማይታወቅ አምላክ›› ብለው ጽፈው ሲያመልኩ ግን የሚያመልኩትን አምላክ ሳያውቁ እንደነበረ ሀዋርያው ቅ/ጳውሎስ አርዮስፋጐስ በተባለው ሥፍራ ቆሞ የክርስትናን ሃይማኖት እንዴት እንደሰበካቸውና የማይታወቀውን አምላክ ሲገልጽ ‹‹ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሠማይና የምድር ጌታ ነውና….›› (የሐዋ 17፡24) በማለት ስለእግዚአብሔር ሀልወት ለአቴና ሰዎች ገልጧል፡፡

የእግዚአብሔር ጠባዮች
የእግዚአብሔር ጠባዮች በሁለት  አጠቃለን ለማየት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው በማናቸውም መልኩ ለእግዚአብሄር እንጂ ለፍጡር የማይነገር የእርሱ የብቻው የባሕርይው መገልጫዎች ናቸው፡፡ እነርሱም በማንኛውም ሁኔታ ውሱንነት የሌለው መሆኑ፣ በራሱ የሚኖር መሆኑ፣ የማንም እርዳት የማያስፈልገው መሆኑ፣ ዘለዓለማዊነቱ አለመለወጡ፣ በሁሉም ቦታ የሚገኝ መሆኑ አለመታየቱ፣ አልፋና ኦሜጋ መሆኑ ወዘተ የመሰሉት ጠባዮች ይገኙበታል፡፡

ሁለተኛው ደግሞ እግዚአብሔር ከፍጥረቱ ጋር ባለው ግንኙነት ላይ የተመሰረተ ነው ይህም ሁሉን ዐዋቂነቱ፣ ጥበበኛነቱ፣ ሁሉን ቻይነቱ፣ ቅዱስነቱ፣ ትክክለኛ ዳኝነቱ፣ ፍቅሩና ደግነቱ፣ እውነተኛነቱና ታማኝነቱ…. ወዘተ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ እነዚህን ሰዎች በጸጋ በተለያየ መጠን ያግኙ  እንጂ የእግዚአብሔር ግን የባሕርይው ናቸው፡፡

ምስጢረ ሥላሴ
የክርስቲያን ሃይማኖት ከሌሎች ሃይማኖቶች ተለይቶ ከሚታወቅባቸው ዋንኞቹ ርዕሶች መካከል ምሥጢረ ሥላሴ ወይም የእግዚአብሔር አንድነትና ሦስትነት እምነት አንዱ ነው፡፡ በክርስትና እምነት መሰረት እግዚአብሄር አንድ ነው አንዱ አምላክ ሦስት አካል አለው፡፡ ይህም ማለት እግዚአብሔር አንድ ሲሆን ሦስት አካል አለው ማለት ነው፡፡

በሌላ አባባል አንድ መለኮት ሦስት አካል፣ ወይም ሦስት አካል ያለው አንድ መለኮት ማለት ነው፡፡ የሥላሴ አንድነት እና ሦስትነት ምስጢር ግልጽ ሆኖ በመጽሀፍ ቅዱስ ተቀምጧል፡፡ ሊቀነቢያት ሙሴ በጻፈው በመጀመሪያ የመጽሀፍ ቅዱስ ክፍል ‹‹እግዚአብሔር በመጀመሪያ ሰማይና ምድርን ፈጠረ›› ( ዘፍ 1፡1) በማለት አንድነቱን ገልጾ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌያችን በአምሳያችን እንፍጠር ( ዘፍ 1፡26) በማለት በአንድ ምዕራፍ የእግዚአብሔርን አንድነትና ሦስትነት በግልጽ አስቀምጦታል፡፡ (ዘፍ 3፡22 ፣ ዘፍ 11፡7፣ ኢሳ 6፡3፣ ዘኑ 6፡24)
ከመጀመሪያው ጀምሮ በሐዲስ ኪዳን ውስጥ ስለአንድነት እና ስለሦስትነት ትምህርት ግልጥ ሆኖ በስም ቀርቧል፡፡ ወንጌላዊው ቅ/ማቴዎስም እንግዲህ ወደ ዓለም ሕዝብ ሁሉ ሂዱ፡፡ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኃቸው የኔ ደቀመዛሙርት አድርጓቸው›› (ማቴ 28፤19) በማለት አስቀድሞ በብሉይ ኪዳን መጽሐፍት ተጽፎ የሚገኘውን የሦስትነቱን ምስጢር በግልጽ በስም ጠቅሶ ይገኛል፡፡(ማቴ 3፡13-17 ፣ ማር1፡19-11፣ ሉቃ 3፡21-22፣ ማቴ17፡5፣ሉቃ 1፡35፣ዮሐ1፡33)

በተለያየ ዘመናት በነገረ መለኮት ላይ ለሚነሱ ክህደት የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የትምህርቱ ስርወ እምነት እንዳይበረዝ በተለይ በኒቂያና በቁስጥንጥንያ ጉባዔያት የሐይማኖት ቀኖናዎች የአንድነቱን፣ የሦስትነትን እምነት አረጋግጠዋል፡፡ ይህም ፀሎተ ሃይማኖት በሚባለው የሃይማኖት ጸሎት ውስጥ ተካቶ ይገኛል፡፡

‹‹ሁሉን በያዘ ሰማይንና ምድርን የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን፡፡›› ይህን ስለ እግዚአብሄር አብ፤ ‹‹ከዘመናት ሁሉ በፊት ከአብ የተወለደ በእግዚአብሔር አንድያ ልጅ በአንዱ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፡፡›› ይህን ስለ እግዚአብሔር ወልድ ‹‹ሕይወትን በሚሠጥ ጌታ፣ ከአብ ከሰረፀ፣ ከአብና ከወልድ ጋር በሚሰገድለት በነቢያት አድሮ በተናገረ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን›› ይህንን ደግሞ ስለ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በቀኖናቸው ደንግገዋል፡፡

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ ክብር

በንጉስ ቁስጢንጢኖስ ዘመነ መንግስት በ325 ዓ.ም በኒቅያ ከተማ በተሰበሰቡት 318 የዓለም ኤጲስ ቆጶሳት ውሳኔ መሰረት ከተወገዘው ከአርዮስ ጀምሮ የጌታችን የባሕርይ አምላክነትና ከአብ ጋር ያለው እኩልነት የሚክዱ የአርዮስ ወገኖች ነበሩ አሁንም አሉ፡፡ ለዚህም ምላሽ ወንጌላዊው ቅ/ዮሐንስ ‹‹ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳችስ ስንኳ ያለእርሱ የሆነ የለም›› (ዮሐ1፡3) በማለት ስለክርስቶስ ክብር ተናግሯል፡፡ ይህም ማለት (ዘፍ1፡1) ሰማይንና ምድርን እንዲሁም በእነርሱ የሚገኙትን ፍጥረቶች ሁሉ የፈጠረው እግዚአብሔር እርሱ ነበር ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ እውራንን ያበራ፣ አንካሳን ቀጥ ያደረገ፣ ዱኩማንን ከድካማቸው ያሳረፋቸው፣ ሙታንን ያስነሳ፣ ህሙማንን የፈወሰ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክ መሆኑን ነቢያት እንደተናገሩት፣ ሃዋሪያት እንደሰበኩት መምህራን እንዳስተማሩት ይልቁንም ራሱ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  እንዳረጋገጠልን ይህንን የሐይማኖት መሰረት አድርገን እናምናለን፡፡ ‹‹የሥጋን ህማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ እግዚአብሔር በባህርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም ሕማም በሚስማማው ባህርዩ ኃይልን እንጂ ሞትም ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በሆነ ጊዜ ሞትን አጠፋ ከሞተም በኋላ ፈርሶ በስብሶ መቅረትን አጠፋ›› (ሃይ አበ.ገጽ 175) ቅዱስ ቴዎድጦስ የዕንቁራ ኤጲስ ቆጶስ፡፡

የመንፈስ ቅዱስ መለኮታዊ ክብር
መንፈስ ቅዱስ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል መሆኑን ቤተክርስቲያን ታምናለች (ታስተምራለች) ይህም ማለት በባህርይ በጠባይና የመለኮት ግብር በሆኑ ነገሮች ሁሉ ከአብና ከወልድ ጋር እኩል ማለት ነው፡፡ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንዱ ከሌላው የሚበልጥ ወይም የሚያንስ ሳይሆን ሦስቱም አካላት በከሃሊነት፣ በክብር በሥልጣን፣ ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም እኩል ናቸው፡፡

የመንፈስ ቅዱስ መለኮታዊ ክብር ከአብና ከወልድ ጋር በባህርይ እኩል መሆኑን ቅዱሳት መጻህፍት በበቂ ማስረጃዎች አረጋግጠዋለሁ፡፡ በቅዱሳት መጻህፍትም በግልጥ የቀረበ በመሆኑ ቤተክርስቲያን ከተመሰረተችበት ጊዜ ጀምሮ በመንፈስ ቅዱስ አካልነት ማለት ከሶስቱ አካላት አንዱ መሆኑን ታምናለች፡፡ ይሁን እንጂ የመንፈስ ቅዱስን መለኮታዊ ክብር የሚክዱ መናፍቃን በተለያዩ ዘመናት ተነስተዋል፡፡ እንደ አርዮስ፣ ሰባልዮስ እና መቅዶንዮስ ያሉ ናቸው፡፡

ለእነዚህም መናፍቃን ሊቃውንት ‹‹ወንአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ማህየዊ ዘሠረፀ እመ አብ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሆ ምስለ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ……›› በማለት በሃይማኖት ፀሎት ደንግገዋል፡፡ ሀዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ይሁን እንጂ ይህን ሁሉ የሚያደርገው ያው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ እንደፈቀደ ለእያንዳንዱ ሰው የተለየ ስጦታን ይሰጠዋል፡፡ (1ቆሮ 12፡11) በማለት የመንፈስ ቅዱስን መለኮታዊ ክብር ገልጧል፡፡ ከላይ ለማየት እንደተሞከረው በነገረ መለኮት ትምህርት ውስጥ ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ያለመጠራጠር ለልጆቿ የሥላሴን አንድነትና ሶስትነት ያለመቀላቀል ያለመለያየት ስታስተምር ኖራለች ወደፊትም ታስተምራለች፡፡

የሥላሴ ቸርነት ከሁላችን ጋር ይሁን  አሜን!!!

አምስቱ አዕማደ ምሥጢር

አምስቱ አዕማደ ምሥጢር

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነት መሠረቶች የሆኑት አምስቱ አዕማደ ምሥጢር (ምሰሶዎች) የሚባሉት ምሥጢረ ሥላሴ፣ ምሥጢረ ሥጋዌ፣ ምሥጢረ ጥምቀት፣ ምሥጢረ ቍርባን፣ እና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን ናቸው።

እነዚህ ምሥጢራት የክርስትና እምነት መሠረት ሲሆኑ፣ የማይታየውን የሃይማኖት ምሥጢር በሚታይ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት የሚገልጹ ናቸው።

የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር  አጭር ገለጻ፦

1.ምሥጢረ ሥላሴ /Mystery of Holy Trinity/
ይኸውም እግዚአብሔር በአካል፣በስም እና በግብር ሦስት እንዲሁም በመለኮት፣በፈቃድ በባሕርይ አንድ (አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ) መሆኑን የሚያስተምር ፍጹም አንድነት እና ፍጹም ሦስትነትን የሚያብራራ ነው።

2.ምሥጢረ ሥጋዌ/Mystery of Incarnation/
ይኸውም እግዚአብሔር ወልድ የሰውን ባሕርይ በመዋሐድ ከድንግል ማርያም ፍጹም ሰው ሆኖ መወለዱን፣ ያለመቀላቀልና ያለመለየት የፈጣሪና የፍጡር ባሕርይ በአንድ አካል መዋሐዳቸውን የሚያስተምር ነው።

3.ምሥጢረ ጥምቀት/Mystery of Baptism/
ይኸውም በዮርዳኖስ ወንዝ በጌታችን ጥምቀት ምሳሌነት፣ በውሃ እና በቃል አማካኝነት ሰው ዳግመኛ የሚወለድበት እና የኃጢአት ሥርየት የሚያገኝበት ምሥጢር ነው።

4.ምሥጢረ ቍርባን/Mystery of Holy Eucharist/
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ ሥጋ እና ደም መሆኑን በማመን፣ ምዕመናን ከክርስቶስ ጋር የሚዋሐዱበትና የዘላለም ሕይወት የሚያገኙበት ታላቁ ምሥጢር ነው።

5.ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን/Mystery of Resurrection of the dead/
ይኸውም በዓለም መጨረሻ የሞቱ ሰዎች ሁሉ አካላቸው ተለውጦና ተቀድሶ በነፍስ ተመልሰው፣ ለፍርድ እንደሚነሡና ከሞት በኋላ ስላለው የዘለዓለም ሕይወት የሚያስተምር ነው።

ሥርዓተ አምልኮ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ

ሥርዓተ ቤተክርስቲያን ስንል “ሥርዓት፣ ቤትና ክርስቲያን” ከሚሉ ሦስት መሠረታዊ የግእዝ ቃላት የሚመሠረት ስያሜ ነው። እነዚህም ቃላት ቁልፍ በመሆናቸው በመጠኑ ልናያቸው ያስፈልጋል። “ቤተ ክርስቲያን፡” የሚለው ሐረጋዊ ቃል፤መነሻው የግእዝ ቋንቋ ሲሆን፤ “ቤተ” የሚለው ቃል ራሱን ችሎ በሁለት ይፈታል። ይህም “ቤተ”= አደረ እና ወገን ሆነ የሚል ነው። “ቤተ” አደረ ተብሎ ሲፈታ ቤተክርስቲያን የሚለው ሐረግ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ የሆነውን እና ለቅዱሱ አምላክና ለቅድስና ዓላማ የተለየውን፣ በሜሮን የከበረውንና የመሰዊያ ታቦት ያለበትን ቅዱሱን ሥፍራ ያሳያል። ይህም ለመንፈሳዊው ተልእኮ መሰብሰቢያ የሆነውን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን1 (ሉቃ. ፩፡፳፩፤ኢሳ.፵፬፡፳፰) ሲያመለክት፤ ሁለተኛው የ”ቤተ” ፍች ደግሞ ፣ ቤተ – ወገን ሆነ2 የሚል ሲሆን፤ የክርስቲያን ወገን ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ቤተ እስራኤል ስንል፦ የእስራኤል ሕዝቦች፣ እስራኤላውያን ማለት እንደሆነ ሁሉ ቤተክርስቲያን ስንልም ክርስቶሳውያን ማለታችን ነው። በዚህም ቤተክርስቲያን የሚለው ሐረግ፦

፩) የክርስቲያኖች አንድነት ወይም ስብስብ (ዕብ. ፲፪፡፩)
፪) የክርስቲያን ሰውነት (፪ ቆሮ. ፮፡፲፮፤ ሐዋ. ፲፩፡፳፮) በሚል ተገልጧል።

በአጠቃላይ ቤተክርስቲያን ስንል፣ በምድር ያለች ለሰማያዊው የምስጋና መቅደስ አርአያ የምትሆን ዳግሚት ኤዶም ወይም የኤዶም ገነት ምሣሌ፤ የእግዚአብሔር መንግሥት፤ ልዩ የቅድስና ቦታ ናት፡፡ ለአምልኮ ወደ ቤተክርስቲያን ስንገባ ከበሩ ላይ ትልቅ መስቀል ይኖራል በተጨማሪም በትእምርተ መስቀል አማትበንና ተሳልመን እንገባለን። በተለይ በቅጽሯ ውስጥ በበስተምሥራቅ ክፍል ብዙ ጊዜ እድሜ ጠገብ የሆኑ አጸዶች ወደሚገኙበት ስፍራ ስንገባ፤ ይህም ቀድሞ ባለመታዘዝ ምክንያት
ከወጣንባት ከኤዶም ገነት በክርስቶስ መስቀል ወይም መታዘዝ ዳግመኛ የመመለሳችን ምሳሌ ነው። ቤተክርስቲያን ተቋም ሳትሆን በምድር ላይ ያለች የማትከፈል አንዲት የክርስቶስ መንግሥት ናት። “ወሶበ ቦእነ ውስተ ጽርህከ ንሔሊ ከመ ንህነ ቀዋምያን በውስተ መንግሥትከ፡፡” 4 ወደ ቤትህ በገባን ጊዜ በመንግሥትህ ውስጥ እንደቆምን እናስባለን። ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የሚገኘው በምድር ቢሆንም የሰማይ አምሳል (Image of the heavenly kingdom) ስለሆነ ሥርዓቱና አምልኮው ፍጹም ሰማያዊ ነው። ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የገባ ሰው በሥጋው በምድር ላይ ስሜቱን ይገልጻል፡፡ በነፍሱ ሲኖር ደግሞ ከነፍሱ ጋር በተዋሐደ መንፈሱ በቁሳዊው ዓለም (material) በአጸደ ሥጋ ካሉት ጋር ይሳተፋል፡፡ የቤተ
ክርስቲያን ምልአት የሚባለው የሰማያውያንና የምድራውያን ሕብረት ሲሆን በአንድነቷ በሥርዓተ ቅዳሴ በምትፈጽመው በምስጢረ ቁርባን የድል ነሺዎች ሕብረት ወይም የቅዱሳን ማሕበር እና እንዲሁም ቅዱሳን መላእክት በመንፈስ አንድነት ይገኛሉ፡፡ ይህ ሁኔታ በግሪከኛ ኮሚኒዮሳንክቶረም ወይንም ካይኖኒክ ሀጊዮን /Communio Sanctorum or Koinoniahagion/ ተብሎ ይጠራል። በቅዳሴው ቡራኬም ካህኑ፦ ልዑል እግዚአብሔር ሁላችንንም ይባርክ በመንፈሳዊም በረከት ሁሉ ያክብረን። ወደ ቅድስት ቤተክርስቲያን መግባታችንንም ዘወትር በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ከሚያገለግሉት ከቅዱሳን መላእክት ጋራ በአንድነት ያድርግ። በየጊዜውና በየሰኣቱም ሁሉ ከሚያመሰግኑት ዛሬም ዘወትርም ለዘለዐለሙ
እንዲል። ስለዚህ አምልኮ ወይም ቅዳሴ በሰማይ የሆነውን ሀገራችንን በምድር እያለን መኖር የምንጀምርበት፣ እና ሰማያዊ የምንሆንበት፤ የመንግሥተ ሰማያትን ጣእም፣ የክርስቶስን ደስታ፣ የምንቀምስበት በምድር ላይ የሚከናወን ሰማያዊ ሥርዓት ነው።

ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ስንል የጋራ ሥራ አገልግሎት በጋራ መፈጸም፣ የቤተ ክርስቲያን እቅድ፣ የቤተ ክርስቲያን አሠራር፣ መርሐ ግብር ደንብ፣ የክርስቲያኖች የሕይወት መመሪያ የክርስቲያኖች የጸሎት ሥርአት፣ የአኗኗር ደንብ፣ የክርስትና ሕይወት የጉዞ መስመር፣ የሚያምኑትን የሚኖሩበት መንፈሳዊ ሕግ ማለት ሲሆን አንቀጸ ንስኃንና የምሥጢራትን አፈጻጸም በሙሉ አጠቃሎ የያዘ መመርያ ማለት ነው። አምልኮ የቤተ ክርሰቲያኒቱ ሁለነተናዊ ሕይወት ነው፡፡ አምልኮ ማለት የምናምነውን በመኖር የምንቀደስበት ማለት ነው። የክርስቶስ ጥሪ “እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” ስለሚል፣ ይህ የሚፈጸመው በአምልኮ በኩል ብቻ ነው። አምልኮ መጽሐፍ ቅዱስን እየጸለዩ መማር፣ እየተማሩ መጸለይ፣ እየጸለዩ መዘመር፣ እየዘመሩ ማመስገን፣ ማለት ነው። “liturgy is the celebration of faith”. ክርስቶስ በምድር ለኛ የከፈለውን ዋጋ እያሰብን በመገዛት ይምናመሰግንበት የምስጋና ሥርዓት አምልኮ ይባላል። ይህም ቅዳሴ ሲሆን፤ በአምልኮ ክርስቲያናዊ ሕብረት መፈጸም
ነው፣ አንድነት ነው፣ ሥርየት ነው፣ ዝማሬ ነው፣ ጸሎት ነው፣ ትምህርት ነው፣ ምስጋና ነው። ቅዳሴ በመገዛት የሚቀርብ ልዩ ሰማያዊ ምስጋና ስለሆነ በምድራዊያን ብቻ ያልሆነ በሕያውያንና ሰማያውያን አንድነት የሚቀርብ ልዩ ሰማያዊ ምስጋና ማለት ነው።

የቤተክርስቲያኒቱ ሁለንተናዊ ሕይወት የሆነው የምስጋና ክንውን ሥርዓት ያለው በመሆኑ ሥርዐተ አምልኮ ይባላል። ሥርአተ ቤተክርስቲያን ስንል ሥርአተ አምልኮ ማለታችን ነው። የአምልኮ ሥርዓት ሥርዓተ ቤተክርስቲያን ነው። ስለዚህ ሥርዐተ አምልኮ ስንል፤ መንፈሳዊ የጋራ ሥራ ማለት ነው ወይም አምልኮን በጋራ በመሆን በሥርዐት መፈጸም ማለት ነው። ሥርዓተ አምልኮ በሌላ አነጋገር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በየጊዜው የሚፈጸም ሰማያዊ አገልግሎት ሲሆን ሥርዐተ አምልኮ ማለት
ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ማለት ነው ይህም የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት ማለታችን ነው፡፡ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ የመጨረሻው የጸሎት ሥርአት ቅዳሴ ይባላል። የሐዲስ ኪዳን ሥርዓተ ኣምልኮ ማእከሉ ክርስቶስ ስለሆነ፤ የምናምነውን በመኖር ከክርስቶስ ጋር አንድ መሆን ማለት ነው። የየትኛውም ቅዱስ ወይንም ሰማእት መታሰቢያ8 በዓል ቢሆን የቅዳሴ አላማው ከክርስቶስ ጋር አንድ መሆን ነው። ለዛ አላማ ስኬት የቅዱሱ በረከት ረድኤትና ምልጃ እገዛ ለመጠየቅ ፍቅር ያስገድደናል። በክርስቶስ ቤዛነት የተዋጁ ክርስቲያኖች ዋና ሥራቸው የተቤዣቸውን በምስጋናና በአምልኮ በዝማሬ ማምለክ ነው። ቅዳሴ የክርስቶስን ሕማም፣ ሞትና ትንሳኤ እያሰብን እግዚአብሔር አብን በአንድ ልጁ በክርስቶስ ሞት ላሳየን ዘለዓለማዊ ፍቅር ምስጋና ምናቀርብበት የኦርቶድክሳዊ የሕይወት መንገድ ነው። እርሱም እናታችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በሉቃስ ወንጌል ም1 “በእኔ ታላቅ ሥራ አድርጓልና ስሙም ቅዱስ ነው” እንዳለች ይህንኑ መለኮታዊ ቃል እያስተጋቡ ስልተደረገው ታላቅ የማዳን ሥራ ቅዱስ የሆነውን ስሙን በማመስገን ጸንቶ መኖር ነው።

የሥርዓተ ቤተክርስቲያን ምንጭ፦ የሥርዓተ ቤተክርስቲያን ምንጩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በዋናነት የተዘጋጀው ለአምልኮ ስለሆነ የአምልኮ መጽሐፍ ይባላል። ከሰማንያ አንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ መካከል በዋነኛነት ስምንቱ የሥርዓት መጻሕፍት በመባል ያታወቃሉ።መጽሓፍ ቅዱስ ሁለተኛም ሦስተኛም ጭማሪ የሌለበት አንድ ነው። ሌሎቹ የሊቃውንት መጻሕፍት የሚባሉት በተለያየ ዘመን ለተነሱ መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጎ ለተነሳው የምንፍቅና ጥያቄ በቂ ምላሽ የተሰጠባቸው ማብራሪያዎች ናቸው። ስለዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያ ልንላቸው እንችላለን። በተጨማሪም እንደ ድርሳናትና ቅዱሳን ገድላት የመሳሰሉትን ስንመለከት ለምሳሌ ገድላት ስንል መጽሐፍ ቅዱስን እንዴት እንደኖሬው የቅዱሱን ሕይውት በማየት በረከት የምናገኝበት በረድኤት ለቅድስና የምንነሳሳበት “የተኖረ ወንጌል” ማለት እንጅ ሁለተኛ መጽሐፍ ቅዱስ ማለት አይደለም።

የሥርዓተ ቤተክርስቲያን አስፈላጊነት፦ አምልኮ ያለሥርዓት ሊከናወን አይችልም። ለአምልኮ ሥርዓት ለምን አስፈለገ ስንል፣ ሁሉም ሥራ ወጥና ዘላቂ በሆነ መልኩ ለመሥራትና ከየት ተነስቶ ወዴት እንደሚሄድ ለመከታተል ሥርዓት ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሃሳብና አንድ ልብ ሆኖ ለማምለክ መንፈሳዊውን ሥራም ለመከታተል ሥርዓት የግድ አስፈላጊ ነው። ያለ ወጥ ሥርዓት፣ እርስ በእርሷ እንደምትለያይ መንግሥት፤ ሳይግባቡ ይቀሩና አንድ ሐሳብና አንድ ልብ ለመሆን አይቻልም። የሃይማኖት ምስጢራትን ለመፈጸም ሥርዓት የሃይማኖት መገለጫ ስለሆነና ማንኛውንም ነገር ወጥና ዘላቂ በሆነ መልኩ ለመሥራት ከየት ተጀምሮ በየት በኩል ሄዶ በየት በኩል እንደሚጠናቀቅ ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት
ይዘጋጅለታል። የአንድ ሥራ አሠራር በትክክል ካልተነደፈና አካሄዱ ካልተስተካከለ፤ ሥራው የተዘበራረቀ ይሆናል ፍጻሜውም አያምርም። ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፤ ብዙ ስንሆን አንድ ልቡና አንድ ሃሳብ እንዲኖረን የሚያደርገን ነውና። /ኤፌ. ፬፥፫፤ የሐዋ. ፬፥፴፪፤ ሮሜ. ፲፭፥፮/።

የሐዲስ ኪዳን ሥርዓተ አምልኮ አፈጻጸም፤ አምልኮ ማለት መገዛት ማለት ነው። መለከ የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙ ገዛ ማለት ነው። አምላክ ወይም መለኮት ስንል ትርጉሙ ፈጥሮ የሚገዛ ገዢ ማለት ሲሆን አምልኮ ማለት ለነፍስና ለሥጋ አስገኝ ለፈጣሪ ሰማያት ወምድር በነፍስና በሥጋ መገዛት ማለት ነው። በኦርቶዶክስ ክርስትና ሥርዓተ አምልኮ እግዚአብሔር በአንድነት በሦሥትነቱ ይመለካል።

በማትከፋፈል አንድነት በማትጠቀለል ሦስትነት ይመለካል። አንድነቱን በማይከፋፍልበት በሦስትነቱ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ወይም ሥላሴ በመባል በ3 ስም በ3 ልዩ አካላትና ገጻት እንዲሁም በ 3 ግብራት፤ ሲመለክ እንዲሁም ሦስትነቱን በማይከፋፍልበት አንድነቱ እግዚአብሔር፥ መለኮት፥ አምላክ ገዢ ፈጣሪ መጋቢ እየተባለ በአንድነቱ ይመለካል።

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዘመነ ሥጋዌ ያከናወናቸው የመስቀል ጉዞዎች ዐበይት ዐበይት ክንውኖች የሥርዓተ አምልኮ መሪዎች ስለሆኑ ዐበይት በአላት ይባላሉ። በሐዲስ ኪዳን በነገረ ድኅነት አስተምህሮ ምስጢረ ሥላሴ በምስጢረ ሥጋዌ ይታወቃልና ሥርዓተ አምልኮው ምስጢረ ሥጋዌን (አምላክ ወሰብእ ሆኖ መውረድ መወለዱን፥ መራብ መጠማቱን፥ መሰደብ መገረፉን፥ መሰቀል መሞቱን፥ መነሳት ማረጉን፥) ማዕከል ያደረገ ነው። በአዲስ ኪዳን የዓለም መስዋእት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። እርሱ ክርስቶስ ስለሁላችን ኃጢአት መስዋእት ሆኖ በመስቀል ላይ የተሰዋ በግ ወይም የሚሰዋ ቁርባን፣ እንዲሁም መስዋእት የሚሰዋ ሊቀካህን እንደዚሁም መስዋት የሚቀበል ሕያው አምላክ ነው።
በዚሁ ላይ ተመሥርቶ ስብሐተ ነግህ የማይደርስበት፥ ጸሎተ ኪዳን የማይጸለይበት እንዲሁም ለዓለም የተሰዋው ኢየሱስ ክርስቶስ በመስዋእት የማይከብርበት፥ ቅዳሴ የማይቀደስበት ዕለት የለም።

ከቅዱሳኑ ጋር ሕብረት ይፈጸማል። የድል ነሺዎች የጻድቃን የሰማእታት የተጋዳዮች ምእመናን። ነገረ ድኅነት ሒደት ነው። ጊታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እለት ተወልዶ እለት ተሰቅሎ የሰውን ልጅ ድኅነት እንዳልፈጸመ ሁሉ ነገረ ድኅነትም ሒደታዊ ነው። ሒደት እንደመሆኑ መጠን የነገረ ድኅነት ክንውኖች በአመቱ ኡደት ውስጥ አንኳር አንኳር ክንውኖቹ ይዘከራሉ ይታሰባሉ። እንደየ ክንውኖቹ ተግባራት አበይትና ንዑሳን ተብለው ከአመት እስከ አመት ባለው ሥርዓተ አምልኮ ማእከል ሆነው በመስዋእት ይዘከራሉ ይህም ዓበይትና ንዑሳን በዓላት ተብለው በሁለት ይከፈላሉ። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኛ ሲል የፈጸማቸውን የነገር ድኅነት የመስቀል ጉዞዎች በተለያየ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን የአምልኮ ርእስ ሆነው የዘከራሉ። በኦርቶዶክሳዊት ሥርዓተ አምልኮ መሠረት እነዚህ የነገረ ድኅነት አንኳር አንኳር ክንውኖች እንደየታሪካቸው ይዘት በጾምና በትፍስሕት ይዘከራል። ለምሳሌ በሰባቱ አጽዋማት ከሚታሰቡት የነገረ ድኅነት አንኳር ክንውኖች መካከል በዕለተ ረቡዕ እና አርብ የሚታሰበው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በምክረ አይሁድ የተፈጸመው የሐሰት ክስ፥ በደቀመዝሙሩ የተከዳበት፥ ይሁዳ በመሳም አሳልፎ ሊሸጠው በ30 ብር የተስማማበት እንዲሁም
የክርስቶስን መከራና የተዋጀንበትን የመስቀል ዋጋ ጌታየ ለኔ ሲል በመስቀል መራራ ሞትን ታገሰ ሲል አፉን እስኪመረው እየጾመ ፍቅሩን በተግባር ይገልጣል። በመገዛት የተዋጀውን አምላክ በተግባር ያመልካል። ይህም ተግባራዊ አምልኮ ይባላል። ሁሉን ትቶ ዝቅ ያለውን ክርስቶስን፤ ያለንን ማድረግ የምንችለውን ሳይቀር በመተው ከጌታው የሚበልጥበት ምንም እንደሌለ በኑሮው ያሳያል። ማድረግ የምንችለውን ትተን መገዛት በተግባር የተፈተነ ፍቅር መገለጫ ነው። ዝቅ ብሎ እየወደቀ እየተነሳ ወደቀደመ ክብራችን የመለሰንን እየወደቁና እየተነሱ በስግደት9 ፍቅሩን ማሰብ የእውነተኛ አምልኮ ማረጋገጫ ነው። ለክርስቶስ ኢየሱስ መገዛቱን በተግባር ያሳያል። ያረጋግጣልም። ጾም መከልከል ነው።

ሌሎቹ ደግሞ በትፍስሕት የሚዘከሩ የነገረ ድኅነት አንኳር ክንውኖች እንደ ትንሳኤ ልደት ጥምቀት የመሳሰሉት ሲሆኑ በተለይ ሞትና መቃብርን ድል ነስቶ የተነሳባት፥ ቅዱስ ዮሐንስ በደሴተ ፍጥሞ በነበረበት ጊዜ በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ10 ስላለ ከሐዋርያት ጌዜ ጀምሮ የጌታ ቀን ሆና በዋናነት መደበኛ የአምልኮ መፈጸመያ የሆነችው፤ በተለይም ቅዱሳን አባቶቻችን በሐይማኖተ አበው “በእሑድ ቀን በጧት እጅግ ማልደህ በሌሊት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሂድ፤ ስትሄድም ልቡናህን በማባከን ወዲያና ወዲህ አትይ፤ በንጹህ ቅዳሴም ጊዜ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን እያሰብክ በፍጹም ፍርሐት ቁም።” ሃይማኖተ አበው ዘሠለስቱ ምእት ፳፡፳፪፬. ብለው ሥርአቱን እንዳጸኑልን፣ የሐዲስ ኪዳን ታላቋ ሰንበት ዕለተ እሑድ ናት። ይህች ዕለት ከዕለታት ሁሉ የላቀችና የተለየች ናት ምክንያቱም ከሌሎች እለታት በተለየ፤ በመንፈስ ሆነን፣ መንፈሳዊ በሆነ ተግባር ተሰማርተን፣ በቅዳሴ የምናከብራት፤ የጸሎትና የሱታፌ ምሥጢራት ዕለት ናት። የጌታ ቀን የተባለችበትም ትልቁ ምክንያት፤ በመስቀል የሞተው ደግሞም ሕያው የነበረው የትንሳኤው ጌታ የክርስቶስ ሞቱና ቅድስት የምቶሆን ትንሳኤውን በመንፈስ ሆነን የምንዘክርበት፤ የአማናዊት እረፍት መገኛ ሆና ለሰው ልጆች ሁሉ የተፈጸመው የመስቀል ጉዞ ፍጻሜ ያገኘባት፣ ክርስቶስ ሞትና መቃብርን ድል ነስቶ የተነሳባት፤ በትንሳኤው የትንሳኤያችን አዋጅ የታወጀባት የድል ዕለት በመሆኗ ነው ስለዚህ ይህች እለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለከፈለው የመስቀል ዋጋ ምስጋና የሚቀርብበት፤ የመስቀል መከራው የትንሳኤውም ደስታ የሚዘከርበት በዝማሬ በምስጋናና በመስዋእት የሚከበር ታላቅ የትፍስሕት ዕለት ነው። የቅዳሴው የምስጋና ጸሎትም “ንዜኑ ሞተከ” “ጌታ ሆይ ሞትህንና ቅድስት የምትሆን ትንሳኤህን እንናገራለን። ዕርገትህንና ዳግመኛ መምጣትህን እናምናለን። እናመሰግንሀለን። እንታመንብህማለን። ጌታችንና አምላካችን ሆይ እንለምንሀለን። እንማልድህማለን።” እንዲል።

ስለዚህ ይህች ዕለት የመስቀል ጉዞውን፣ የተከፈለውን ዋጋ፣ ትንሳኤውን እያሰብን በቅድስት ቤተክርስቲያን በአንድነት ሆነን፣ በሰማይ የሆነውን ሀገራችንን በምድር እየኖርን ትንሳኤያችንን ተስፋ የምናደርግባት፣ በክርስትና ጉዟችን ታላቅና አምስቱን11 መስዋእቶች የምንሰዋባት ዕለት ናት። ከእርሱ ጋር አንድ ሆነን ሕያው የምንሆንበትን12 ሥጋውን ደሙን የምንቀበልበት፣ በሰማያውያን ሕብረት፣ በመላእክት ርደት13፣ በመንፈስ ቅዱስ ርበት14፣ በክርስቶስ ውሕደት፤ በምሥጢራት እየዋኘን የጌታን ደስታ የምንቀምስባት፤ በዝማሬ ሰማያዊነታችንን እያረጋገጥን በሰማያዊ ከፍ ያለ ኅሊና የምንተጋበት ዕለት ናት። በቅዳሴ ጸሎት በመሳተፋችን፤ ለበደላችን ይቅርታና ምሕረት የምንጠይቅበት፣ “እግዚኦ ተሣሃለነ” አቤቱ ይቅር በለን “ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ…” አቤቱ በመንግሥትህ አስበን “እኔ” ብለን ሳይሆን “እኛ” በምልጃ ጸሎት ከፈጣሪያችን ጋር የምንገናኝበት፣ የኃጢአት ስርየት፤ በረከተ ሥጋም በረከተ ነፍስም የምናገኝበት ነው። ከሁሉም በላይ በቅዱስ ሥጋውን በክቡር ደሙ አማካኘነት ክርስቶስ ጋር አንድ ሆነን በመስቀሉ ለታጨንለት ዘለዓለማዊ ሕይወት የምንዘጋጅበት፤ በምድር ላይ እየኖርን ሰማያውያን ይምንሆንበት15 በመስቀሉ ለተጋበዝንበት የእግዚአብሔር መንግሥት አካል
የምንሆንበት ሥርዓት ነው። ያለቅዳሴ የሚዘከር የነገረ መስቀል ጉዞም ሆነ የነገረ ድኅነት ክንውን የለምና እያንዳንዱ ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጸመው በቅዳሴ ነው። ቅዳሴ ማለት “ቀደሰ” ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ምስጋና ማለት ነው። በግእዝ ቋንቋ ምስጋናን የምንገልጥባቸው በቁጥር 11 የሚሆኑ ቃላትን እናገኛለን። ቀደሰ/ቅዳሴ፣ አእኮተ/አኮቴት፤ ወደሰ/ውዳሴ፤ ሰብሐ/ስብሐት፤ ዘመረ/ዝማሬ፤ ሀለየ/ማህሌት፟፤ ባረከ/ቡራኬ፣ ገነየ/ግናይ፣ ለጠነ/ምልጣን፣ ቀነየ/ምቅናይ፣ መዝገነ/ምዝጋን እያለ ይቀጥላል16። ቅዳሴ የሚለው ቃል ግን ሁሉንም የምስጋና ዓይነቶችን አጠቃሎ የያዘ ሰፊ ቃል በመሆኑ “ልዩ ምስጋና” ተብሎ ይተረጎማል።

ቅዳሴ ማለት የመንፈስ ሕግ መፈጸሚያ ነው። ቅዳሴ በየጊዜው የሚፈጽም ይህም በካህኑ መሪነት፣ በዲያቆኑ አስተባባሪነትና በምእመናኑ ተሳታፊነት የማኅበር ጸሎት ለእግዚአብሔር በማቅረብ የጋራ አምልኮ መፈጸም ማለት ነው፡፡ ቅዳሴ እኛ ኦርቶዶክሳዊያን ክርስቲያኖች የሁለነታናዊ ሕይወታችንና የቤተክርስቲያናችን ራስ በሆነው በክርስቶስ ራስነት ሥር በአንድ አካልነት የሚያቀርቡት ነፍስን ደስ የሚያሰኝ ልብን የሚነጥቅ ሰማያዊና የነፍስ ምግብ ነው። ቅዳሴ በተመስጦ እና በጽሞና ሆነን በምሥጢራት ሱታፌ በኩል የእግዚአብሔርን ድምጽ የምንሰማበት፣ እግዚአብሔርን የምናውቅበት ቅዱስ ሥርዓት ነው። ቅዳሴ፤ የመንፈሳዊነት እድገትና ሕይወትን ከመንፈስ ቅዱስ፣ የምንማርበት ትምህርት ቤት ነው። ቅዳሴ አኮቴተ ቁርባን ብሎ የሚቀርብ ምስጋና ስለሆነ ልብንና አእምሮን ከእግዚአብሔር ጋር በማገናኘት፣ ሥጋንና ነፍስን አስተባብሮ በመገዛትና በአንቃድዎ ኅሊና የሚቀርብ የመንፈስ አምልኮ ስለሆነ በአንክሮ፣ በተዘክሮ፣ በአንቃእድዎ፣ በንጹሕ ልቡና፣ በሰቂለ ሕሊና የሚፈጸም አምልኮ ነው። ሞቱና መከራው ጭምር የሚታሰብበት በመሆኑ፤ ከስሜታዊነት ይልቅ በመንፈሳዊነት፤ ከመንዘፍዘፍና ከመወራጨት ይልቅ በስክነት፤ በመፍራትና በመንቀጥቀጥና በረአድ የሚከናውን ነው። ስለሞቱ
ስለግርፋት ስለስቅላቱ ስናስብ እንደቅዱስ ዮሐንስ በመንፈስ ሆነን ነውና።

ከእግዚአብሔር ጋር ምሥጢራዊ አንድነትን ማሳደጊያ ሰማያዊ የሕይወት መንገድ ነውና በሥርዐተ ቅዳሴ የሚጠቃለሉ የአገልግሎት ዓይነቶች …ሥርዐተ ጸሎት (ምስጋና ልመናና ምልጃ)፣ ስብከተ ወንጌል፣ የአምልኮ ስግደት፤ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መሳተፍ/ ሱታፌ፣ ክብር ይእቲ፣ ዝማሬ እና እጣነ ሞገር ናቸው፡፡ በካህኑ መሪነት፣ (ይካ) በዲያቆኑ አስተባባሪነትና (ይዲ) በምእመናኑ ተሳታፊነት ይሕ) የማኅበር ጸሎት በአንድነት ለእግዚአብሔር በማቅረብ አምልኮ መፈጸም ማለት ነው፡፡
በስተመጨረሻም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መሳተፍና ለክርስቲያን ሕይወት የሚሆነውን የመንፈስ ቅዱስ ሀብት መቀበል ማለት ነው፡፡

በሥር ዓተ አምልኮ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚደረግ ክብርና ዝግጅት እንዲሁም ጥንቃቄ

በቅዳሴ ጊዜ መቀመጥ ማውራት የግል ጸሎት መጸለይ ክልክል ብቻ ሳይሆን ነውር ጭምር ነው። ምክንያቱም “እዩኝ ከሁላችሁም ጸሎት የኔ ይበልጣል” ብሎ እንደመታበይ ስለሆነ በኅብረት የሚጸለይ የኅብረት ጸሎት ማለት ነው፡፡ በምድር ባለች ሰማያዊት መንግሥት ለፈጣሬ ሰማያት ወምድር ለእግዚአብሔር የሚቀርብ ሰማያዊ ምስጋና ስለሆነ ቀጥ ብሎ በመቆምና ስግዱ ሲል በመስገድ የሰውነት መስዋእት የሚቀርብበት ነው። ለቅዳሴ ስትዘጋጁ ወደቀራኒዮ እየተጓዛችሁ ስለሆነ 5ቱን የስሜት ሕዋሳት አስገዝተው 5ቱን መስዋእት እየሰዉ በምድር እያሉ ሰማያዊነታቸውን የሚያውጁበት ሥርዓት በክርስቶስን ስቅለት በመስቀሉ ሥር በእለተ አርብ የመገኘት መንፈሳዊ ሥርዓት ነውና ያችን የጭንቅ የአርብ ስቅለትን ከ 6 እስከ 9 ሰአት በመስቀል ላይ የቆየባትን የ3 ሰአት የጭንቅ ቆይታ በማሰብ ለኔ ሲል ተጨነቀ በማለት ለ 3 ሰአታት ያህል በጽሞና የምናስባት ጊዜ ናት።

አገልጋይ ካህናትም የሰማያዊ ሥርዓት አምባሳደሮች ስለሆኑ ሰማያውያን ናችው፡፡ ምክንያቱም ቅዱሳን መላእክት ለእግዚአብሔር ንጹሕ ምስጋና ያለማቋረጥ ለማቅረብ እንደተፈጠሩ ሁሉ፤ አገልጋይ ካህናትም መንፈሳዊ አምልኮን ለመፈጸም የተለዩ ናቸው ሌትና ቀን ለእግዚአብሔር ያለማቋረጥ ምስጋና ያቀርባሉና፡፡ ስለዚህ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ጠንቅቆ ማወቅ እና መንፈሳዊ መልእክቱን ከፍ ባለ ዕውቀት ተረድቶ ማስረዳት፣ የካህናት ተቀዳሚ ተግባር ነው። ስለዚህ በላቀ መንፈሳዊነትና በሰማያዊት ክህነት፣ በትጋት በመጸለይ ቸርነቱን ያለማቋረጥ በማሰብ፣ በማድነቅ፣ እንዲሁም ለዐለም የምስራቹን ቃል መግለጥና ማስተማር፤ አምልኮው እንዲከናወን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። “ብዙ ከሰጡት ብዙ
ይጠበቅበታል”ና፣ ካህናትም በዚህ ሰማያዊ ክብር ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ በክህነት ተጠርተዋልና ሀይማኖትን ከምግባር አዋህደው፣ እውቀት መንፈሳዊና ሥጋዊ ጭምር አደላድለው፣ ጸንቶ ለማጽናት፣ የተሾሙ የእግዚአብሔር መንግሥት ሰራተኞች ናችሁና በምድር አስራችሁ በሰማይ የምታጸኑ በምድር ፈታችሁ በሰማይ የምታስምሩ፣ መራራውና ጣዕም አልባው ዐለም የጣፈጠባችሁ የዐለም ጨው፣ ተላውያነ ሐዋርያት ናችሁ። በአምልኮ በኩል የሰውን ልጅ መንፈሳዊ ሕይወት በመገንባትና የድኅነት ስጦታን ተሳታፊ እንዲሆኑ ነፍሳትን ከዐለም እየነጠቁ ለክርስቶስ፣ በከርስቶስ መማረክ ነው።

በሥርአተ አምልኮ 3 ዋና ዋና አካላት ይገኛሉ እነርሱም ካህናት ዲያቆናትና ምእመናን18 ናቸው። ካህናትም ሆኑ ምእመኑ በሥርአተ አምልኮ የየራሳቸው ድርሻ ስላላቸው መጽሐፈ ቅዳሴ “ይካ” ይበል ካህን “ይዲ” ይበል ዲያቆን “ይሕ” ይበል ሕዝብ እያለ ድርሻ ድርሻውን ያስቀምጣል። በዚሁ መሠረት የከህናት ድርሻ በክህነት በእውቀትና አራያነት ባለው በፍም መንፈሳዊነት አምልኮውን ይመራል። ዲያቆኑ ደግሞ ቅዳሴውን ይራዳል። ጸልዩ፣ ተንሥኡ፣ ስግዱ፣ ፃኡ፣ አውስኡ፣ ነጽሩ…… እትዉ (10ጊዜ) እያለ ያስተባብራል፡፡ የምእመናን ድርሻ19፤ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማድመጥ፣ በምስጢራት ተሳትፎ መክበርና ቅዳሴው እስከሚፈጸምና እትዉ በሠላም የሚለው የማሰናበቻ ዜማ እስኪሰማ መታገስ ናቸው።

ስህተት

– ወኢሰምዐ = የሚነበቡትን ቅዱሳት መጻሕፍት ያልሰማ
– ወኢተዐገሠ= ቅዳሴው እስኪያልቅ መታገስ ያልቻለ
– ወኢተመጠወ= ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበል ያልቻለ

በደል
– እስመ አማሰነ ሕገ እግዚአብሔር = የእግዚአብሔርን ሕግ አጠፋ
– ወአስተሐቀረ ቁመተ ቅድመ ንጉስ ሰማያዊ ንጉሰ ሥጋ ወመንፈስ= የሥጋና የመንፈስ ንጉሥ
በሆነው ሰማያዊ ንጉሥ በሆነው በክርስቶስ ፊት መቆምን አቃሏልና

ቅጣት
– ይሰደድ እምቤተ ክርስቲያን ከቤተክርስቲያን ይለይ።

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚፈጸሙ ምሥጢራት ድኅነታችንን በጥንቃቄ የምንፈጽምባቸው ሃይል መንፈስ ቅዱስ የምንሞላባቸው እንዲሁም ለባሴ ክርስቶስ ወይም ሱታፌ አምላክ ወደመሆን የምናድግባቸው መንፈሳዊ ኃይላት ናቸው፡፡ በቅዳሴ የማይሳተፍና የክርስቶስን ሥጋና ደም የልተቀበለ ሰው በቤተ ክርስቲያን ኅብረት ውስጥ ስለሌለ የክርስቶስ አካል አልሆነም ቢሆንም አልጸናም አልጠበቀምም ማለት ነው። ቅዳሴ በቁሳዊ ዓለም ላይ በሚታይ ሥጋ ቆሞ በመንፈሳዊ ዓለም ውስጥ
በተመስጦ መገኘት ነው። የሰው ልጅ በሁለቱም ዓለሞት በአንድ ጊዜ መኖር የሚችለው በምስጢራት በኩል ባለው ተሳትፎ ነው፡፡ ይህም በቅዳሴ ጊዜ የምትታየው (Visible church) በመንፈስ በሰማይ ካለችው ከማትታየው (invisible) ከሆነችው ቤተ ክርስቲያን ራስ በሆነው በክርስቶስ ተገናዝበው ህብረት አንድነት ይሳተፋሉ ማለት ነው። ቅዳሴ ክርስቶስን ማዕከል አድርጎ በክርስቶስ ራስነት አካል ሆኖ መኖር ነውና። (ዮሐ 15፥2) ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ራስ የሆነላት የክርስቶስ መንፈሳዊ አካል (The spiritual body of Christ) ናትና። (ኤፌ 5፥23) ይህም አንድነት (Christian unity) እውን የሚሆነው የኅብረቷ ምስጢር በሆነው በቅዱስ ቁርባን (Holy Communion) ብቻ ነው።

ኦርቶዶክሳዊ አምልኮ ዋና ግቡ ሱታፌ አምላክ ነውና በጥምቀት ያገኘነው ልጅነት፣ በምሥጢረ ቁርባን በምናደርገው ኅብረት (ዮሐ.15፥4-7)፣ ከክርስቶስ ጋር ያለን ኅብረት በሱታፌ አምላክ (የመለኮታዊ ባሕርይ) ተካፋይነት(2ጴጥ 1፥4) የሚያደርሰን የሕይወት ስንቅ ነው። አንድ ስለምታደርግ ሥጋውና ደሙ እግዚአብሔር አንድ ያደርገን ዘንድ” በዲያቆኑ የሚጸለየው በእንተ ቅድሳት ያስረዳናል። መንፈሳዊ ሕይወት የማይቋረጥ የእድሜ ልክ ጉዞ ነው። በዚህ ዘለአለማዊ ጉዞ የክርስቶስ ሥጋና ደም መንፈሳዊ ኃይል የሚሰጠን ስንቃችን ሆኖ ቀረበልን24። ምሥጢረ ቁርባን ለመንግስተ ሰማያት የተገባን የምንሆንበት፤ የሰው ልጆች የዘላለም ሕይወትን የምናገኝበት፣ በክርስቶስ ቤዛነት ያገኘነውን ነፃነት በሥጋዊ ድካም በኃጢአት ስናሳድፈው ደግሞ ለዘለዓለም ሕያው ከሆነ መስዋዕት በመንፈስ ቅዱስ ጸጋን የምንካፈልበት ታላቅ ምሥጢር ነው። ያለ ምሥጢረ ቁርባን ምሥጢረ ጋብቻም ሆነ ምሥጢረ ንስሐ አይጸናም። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተግባራዊ ትምህርት በአጽኖዖት ያስተማረን ጽኑእ የእምነት መሠረት ነው። ዮሐ.6፥41-60፣ ማቴ. 26፥26-28። ለማጠቃለልም ሐዋርያው “1ኛ ቆሮንቶስ 9 ታገኙ ዘንድ ሩጡ።²⁵ የሚታገልም ሁሉ በነገር ሁሉ ሰውነቱን ይገዛል፤ … እኛ ግን የማይጠፋውን። ስለዚህ እኔ ያለ አሳብ እንደሚሮጥ ሁሉ እንዲሁ አልሮጥም፥ ነፋስን እንደሚጎስም ሁሉ እንዲሁ አልጋደልም፤ ²⁷ ነገር ግን ለሌሎች ከሰበክሁ በኋላ ራሴ የተጣልሁ እንዳልሆን ሥጋዬን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ።” ማሕሌት ወይም መዝሙር ቆመው አድረው ቅዳሴውን አቋርጠው በመውጣት የማያስቀድሱ መዘምራን፤ በአምልኮ ሳይሳተፉ አስቀዳሹን ሊያስተምሩ ቅዳሴው ሲያልቅ ዓውደ ምሕረት ላይ የሚከሰቱ ሰባክያን፣ እንዲሁም ሳያስቀድሱ በስተመጨረሻ ከየአዳራሹ ለዝማሬ ብቅ የሚሉ መዘምራንና ሰንበት ተማሪዎች እና የማያስቀድሱና የማይቆርቡ ምእመናን። ይሰደድ የሚለው ቃል በዋነኛነት ይመለከታቸዋል።

በቅዳሴ ጊዜ በቅዳሴ ጊዜ የሚስቅ ሰው ቅዱስ ባስልዮስ በጻፈው በ፸፪ኛው አንቀጽ ካህን ቢሆን የሚያቀብል ነውና ሥጋ ወደሙን ከተቀበለና ካቀበለ በኋላ ወጥቶ አንድ ሱባዔ ይቀጣ ይጹም ይስገድ፣ ምእመን ቢሆን ግን ሥጋ ወደሙን ሳይቀበል ያን ጊዜ ፈጥኖ ይውጣ ይላል። ምክንያቱም ካህኑ በቅዳሴ ጊዜ ቅዳሴውን ጥሎ ወጥቶ ሲሄድ መጥፎ አብነት እንዳይሆን ነው። ምዕመኑ ግን ሲስቅ ሁሉ ያየዋልና ለሌላ መቀጣጫ እንዲሆን፤ በቤተ መቅደስ የማይወደድ ሌላ ነገር አይናገር፤ በቤተ መቅደስ ጭንቅ፣ ደዌ ሳያገኘው አንዱን ስንኳ ምራቁን እንትፍ አይበል። ነገር ግን ደዌ ቢያስጨንቀው ድምፅ ሳያሰማ ምራቁን በመሐረቡ ተቀብሎ ያሽሸው።

በጸሎትና በአምልኮ የሚሳተፉ ባልና ሚስት ከተራክቦ መከልከል አለባቸው፡፡ (ዘጸ 19፡15) (1ቆሮ 7፡5-7) (ኩፋ 34፡12)። በማሕበር ጸሎት ለመሳተፍ የማያስችል እንደ ደም የሚሸት ቁስል ኃይለኛ ሳል የወር አበባዋ እና እንዲሁም በወንዶች ልማድ ሕልመ ሌሊት ወይም ተጻውሮ የመሳሰሉት ሲከሰቱ እስኪነጹ ድረስ መሳተፍ አይቻልም። በአምልኮ ሰአት በጸጥታ የሚነበበውን የሚተረጎመውን መስማት ተሰጥዖ መቀበል ይገባል እንጅ ወሬ ማውራት ማውካካት መንጫጫት ነውር ነው፡፡ ማንም ማን ዋዛ ፈዛዛ የሚናገር አይኑር፣ ቤተ ክርስቲያን በፈሪሃ እግዚአብሔር ሆነው የሚጸልዩባት የጸሎት ቦታ ናትና ቅዳሴው ሳይፈጸም አቋርጦ መውጣት አይቻልም፣ በጣም ጭንቅ ወይም በሕመም ምክንያት ካልሆነ በቀር። በቅዳሴ ጊዜ ካህናት የሚቀድሱባቸው አልባሳት ነጫጭ ይሁኑ። የመጋረጃ ቀለሞችም በዐበይት በአላት ነጫጭ እንዲሁም በዘወትር ቀይ በሰሙነ ሕማማት ደግሞ ጥቁር ብቻ ነው። እነዚህም በዘፈቀደ ሳይሆን ምሳሌ ስላላቸው ነው።

አንድ ሰው እንኳ ጫማ አድርጎ ከቤተ መቅደስ አይግባ ልዑል እግዚአብሔር የምትቆምባት ደብረ ሲና የከበረች ናትና ጫማህን አውልቅ ብሎ ለሙሴ ተነግሮታልና። /ዘጸአት ፫-፭/ ።

በቅዱስ ቁርባን ጊዜም አስቀድሞ ሊቃነጳጳሳት፣ ጳጳሳት፣ ኤጲስ ቆጶሳት ይቀበላሉ፤ ቀጥሎ በቁምስና መዓርግ ያሉ መነኮሳት፣ ቀጥሎ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት ይቀበላሉ፤ ቀጥሎ ወንዶች በአርባ ቀን የሚጠመቁ ሕፃናት ከሁሉ አስቀድመው ይቀበሉ የዕለት ሹማምንት ናቸውና በንጽሐ ጠባይእ መላእክትን ይመስላሉና። ከነዚህ ቀጥሎ ከአርባ ቀን በኋላ እስከ ስድስት፣ ሰባት ዓመት ያሉት ሕፃናት ትንሾቹ በፊት እየሆኑ እንደየዕድሜያቸው ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው /ክህነት የሌላቸው/ በድንግልና ኑረው የመነኮሱ ደናግል ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው ሃያ፣ ሃያ ሁለት ዓመት የሆናቸው ደናግል ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው በሹመት ያሉ ናቸውና ንፍቀ ዲያቆናት፣ አናጉንስጢሳውያን፣ መዘምራን ይቀበላሉ፤ ከዚያ ቀጥለው የንስሐ ሕዝባውያን በየመዓርጋቸው ይቀበላሉ።

በሴቶችም በኩል ከሁሉ አስቀድሞ የተጠመቁ የሰማንያ ቀን ሕፃናት ይቀበላሉ የዕለት ሹማምንት ናቸውና በንጽሐ ጠባይእ መላእክትን ይመስላሉና፤ ከነዚያ ቀጥሎ ከሰማንያ ቀን እስከ ስድስት፣ ሰባት ዓመት ያሉ ሕፃናት እንደየዕድሜያቸው ሕፃናቱ አስቀድመው ታላላቆች ቀጥለው ይቀበላሉ፤ ከዚያ ቀጥለው አሥራ ሁለት፣ አሥራ አምስት የሆናቸው ደናግል ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው የቀሳውስት ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በሕግ ኑረው የመነኮሱ እናቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያው ቀጥለው የዲያቆናት ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በንሰሐ ተመልሰው የመነኮሱ መነኮሳት እና መነኮሳይያትይቀበላሉ፤ ከነዚያ በኋላ የንፍቀ ዲያቆናት፣ የአናጉንስጢሳውያን፣ የመዘምራን ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በሕግ ጸንተው ያሉ ሕጋውያን እናቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው የንስሐ ሕዝባውያን ሚስቶች በየመዓርጋቸው ይቀበላሉ። ከዚህ በኋላ ካህኑ ሥጋ ወደሙን በፈተተበት እጁ ሕዝቡን ፊታቸውን ይባርካቸው። ቀሳውስት ግን እጅ በእጅ ተያይዘው እርስ በርሳቸው ይባረኩ። ቀዳሹ ካህን ቀሳውስትን ሲያሳልም “የጴጥሮስን ሥልጣን ባንተ አለ” ይበል፣ ተሳላሚው ቄስም “መንግሥተ ሰማያት ያውርስህ ከሾመ አይሻርህ” ይበል። ለዲያቆናትም “ልዑል እግዚአብሔር ያክብርህ ይባርክህ፣
ለማስተማር ዓይነ ልቡናህን ያብራልህ፣ ምሥጢሩን ይግለጥልህ” እያለ ይባርካቸው። ለምዕመናንም “ልዑል እግዚአብሔር ያክብርህ፣ ይባርክህ፣ ገጸ ረድኤቱን ይግለጽልህ” እያለ ይባርካቸው። ለሴቶችም “ልዑል እግዚአብሔር ይባርክሽ፣ ያክብርሽ ገጸ ረድኤቱን ይግለጽልሽ” ብሎ በእጁ ይባርክ።

በአባ ጌዴዎን ብርሀነ መነኮስ ዘደብረ ሊባኖስ
የረዳን ሁሉን ያከናወነ አምላክ ስሙ ይክበር ይመስገን።

20/01/2018 ዓም